መተዋወቂያ

መተዋወቂያ:-  የኢትዮጵያ ስም ትርጉምና ታሪካዊ አሰያየም

እኛ ኢትዮጵያውያን በማንነታችን የምንኮራ ሕዝቦች
ሳለን ታሪካችን ተደብቆብን በመኖሩ ብዙ
ተደናግረናል። ለምሳሌ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ
ብትጠይቁት በአገሩ ይኮራል ግን ስያሜው ከየት
እንደመጣ ወይም ትርጓሜውን ባለማወቁ አንዴ
አቢሲንያነህ ሲሉት ሲያሻቸው ደግሞ ቆዳቸው
በጸሃይ የተቆረ ማለት ነው ሲሉት እሺ ብሎ
ለመቀበል ሲገደድ ኖሯል። ትክክለኛው የኢትዮጵያ
መጠሪያ ታሪኩ ግን እንደሚከተለው በጥንታውያን
መጽሐፍቶቻችን በመጽሐፈ ሱባኤ ተመዝግቦ
ይገኛል፤ እነሆ።

የሳሌሙ ንጉስ ጻድቁ መልከ ጽዴቅ አብርሃምን
ከባረከው በኋላ አብርሃም አስራት ከፍሎ በሰላም
ወደ ኬብሮን ተመለሰ። (ኦ. ዘ. 14:18-20 )
እንዲህም ሆነ የእግዚኣብሔር ካህን መልከ ጸዴቅ
ሶስቱን ልጆቹን ይዞ ሃሎ ወደተባለ ቦታ በመሄድ
ለእግዚአብሔር የእህል መስዋት አቀረቡ።
ልጆቹም እጣ ክፍላቸውን ያውቁ ዘንድ ከአብርሃም
የተቀበሉትን እንቆአርያ (ዛጎል)፥ ህብስት ይዞ
የነበረውን ሞሰበ ወርቅ፥ እና ወይን ይዞ የነበረውን
የወርቅ ጽዋ እጣ ተጣጥለው ተካፈሉት።
እንቆአርያውም ለመጀመሪያ ልጁ ኢትኤል፥ የወርቅ
ጽዋው ለሁለተኛው ለሳሙኤል፥ መሶበ ወርቁም
ለሶስተኛው ለአበመሌክ ደረሳቸውና ሁሉም
ድርሻቸውን ወሰዱ።

መልከ ጽዴቅም በመንፈስ ተሞልቶ ትንቢቱን
በእነርሱ ላይ ተናገረ፤ እንዲህም አለ፥ አንተ የግዮን
ውሃ የምትጠጣና ግዮን በሚፈስበት ምድር
የምትኖር እንቆአርያ የደረሰህ ኃያል ሆይ ለሰላሙ
ንጉስ እና ለካህናት አለቃ ለቸሩ ጌታ የደረሰህን
እንቆአርያና እጣ ክፍልህ ከሆነው ምድር
የምታገኘውን እንቀኦጵና የከበረውን ሉል፤ ከወርቅ
ሐመልማል የተሰራውን በፍታ ገጸበረከት ብለህ
አቅርብለት። እጥዓንም አምጥተህ መድኃኒት ህ
ይሆን ዘንድ አጢስለት ስሙንም አንተ ክርስቶስ ነህ
ብለህ ጠርተህ ለክብሩ ስትል ቀድስ። ፊቱ
ተንበርክከህ ስገድለት አለው።

ኢቴልም ክርስቶስ የምትለው የሰላሙ ንጉስ
መጥቶ የሚነግስበት ቀንና ጊዜው መቼ እንደሆነ
እርሱ ከማን ዘር እንደሚመጣና በየት እንደሚነግስ
ወይም የመምጫውን ጊዜ እንዳውቀው ለይተህ
ንገረኝ አለው።

መልከ ጼዴቅም እርሱ ራሱን የሚገልጽበት ዘመኑ
እስኪደርስ ድረስ እንቆአርያውን በየአመቱ
ተመልከተው። ዘመኑ የራሃብና የቸነፈር ዘመን
ሲሆን መልኩ ይዝጋል። እንደአንተም ይጠቁራል።
የእህልና የበረከት ዘመን ሲሆን ይጠራል፤ ነገር ግን
የንጋቱ ኮኮብ ብርሃን ነጸብራቅ በሆነ ጊዜ ጊዜው
እንደደረሰ ታውቃለህ። የብርሃኑ ጨረርም አገሩን
ያመለክት ሀል። እርሱም እንዳንተ እርሱ ባለበት
ላይ መጥቶ ሲሰግድለት ታያለህ። ይህ ሁሉ
ይፈጸማል፤ ለልጅ ልጅህ እንዲተላለፍና በልባቸው
እንዲጽፉት ለአስተዋይ ልጆህ በአንደበት ህ
ንገራቸው።

ግዮን ከሚፈስበት ጀምረህ እስከ
ምንጩ ባለው ምድር ንገስ፤ ክህነትህንም ጠብቅ
አምላክህንም ለዘላለም ቀድስ አለውና ከአርባ
ዘጠኝ ካህናት ጋር ሾሞ ወደ ምድያም ምድር
ሰደደው። ኢቴልም ከሃሎ ተነስቶ ሲን ምድር
ደረሰ።

ክዚያም በእግዚአብሔር መንፈስ እየተመራ
ከሲን ተነስቶ በአራት መቶ ቀኑ አንኤል የተባለውን
የግዮን (አባይ) ወንዝን ተከትሎ ከምንጩ ደረሰ።
በዚያም ምድር ኢያስጲድያና ዮጵ የተባለ ወርቅ
ይገኝበታል። እርሱም ኢትኤል መባሉ ቀረና ስሙ
ለዘላለሙ ኢትዮጵ ተባል። እርሱም ግዮን
የሚያስገብራቸውን ወንዞች የፈለቁበትን ምድር
በስሙ ኢትዮጵያ ብሎ ሰየመው። ትርጉሙም
ለእግዚአብሔር የሚሰጥ (የተሰጠ) የወርቅ ስጦታ
ማለት ነው። በአባይ ምንጭና በረጅሙ ተፋሰስ ላይ እግዚአብሄር ያነገሰው ኢትኤል በሁዋላ ኢትዮጵ ተባለ:: ይህ የመልከጼዴቅ የበኩር ልጅ ነው የመጀመሪያዉን ማንበቢያና መጻፊያ የሆነዉን የዓማርኛ ፊደል የቀረጸውና ኢትዮጵያን ያቀናው።

 

የዛሬይቱዋ ኢትዮጵያ በሰሜን ምስራቅ የአፍሪካ ቀንድ የምትገኝ አገር ናት፡፡ ጠቅላላ የቆዳ ሰፋት በአሁኑ ሰአት 1.1 ሚሊዬን ካሬ ሲሆን ኣምስት የተላያዩ የአየር ንብረቶች ትልልቅ ዥረቶች (ወንዞች)ና በርካታ ሐይቆች አሏት፡፡

መልክአ ምድር

ኢትዮጵያ የተለያዩ መልክአ ምድር ያላት አገር እደመሆኗ የተለያዬ አየር ንብረት አፈር እንስሳትና ዕፅዋት የሚገኝባት አገር ናት፡፡ ኢትዮጵያ በጣም ከፍተኛ የሆኑ  አምባ የሚባሉ ቦታዎች፤ ስምጥ   ሸለቆዎች፤ በገመገም ዉስጥ ጠልቀዉ የሚፈሱ ትልልቅ ወንዞችና ሰፋፊ ሜዳዎች በውስጧ ይዛለች፡፡ ከባህር ወለል በላይ 4620 ሜትር ከሚደርሰው ራስ ዳሽን ተራራ እስከ 148 ሜትር ከባህር ወለል በታች እስከሆነው የዳሎል ስርጉድ (ዲኘረሽን) መሬትን ጨምሮ ዉርጭ ደጋን ወይና ደጋን ቆላንና በረሃን የተጎናጸፈች ሀገር ናት፡፡

ኢትዮጵያ ብዙ  ትላልቅ እንደ አባይ ዠማ ዎንጪት ግቤ ተከዜ አዋሽ ኦሞ ዋቢ ሸበሌና ባሮ-አካቦ የመሳሰሉ  ወንዞችን የታደለች አገር ናት፡፡

ከሜዲትራንያን ምስራቃዊ ክፍል ተነስቶ፣ እስከ ደቡብ ምስራቅ አፍሪካ የምትገኘው ሞዛንቢክ ድረስ የሚደርሰው ታላቁ የስምጥ ሸለቆ ኢትዮጵያን ለሁለት ከፍሏት ያልፋል፡፡

የአየር ንብረት

ኢትዮጵያ እንደ መልክአ ምድራዊ አቀማመጧ የአየር ንብረቷም በተለያዩ ቦታዎች የተለያየ ሁኔታ ይታይባታል፡፡ የመካከለኛው ከፍተኛ አካባቢ ብዙም የማይፈራረቅ ወይናደጋማ አይነት የአየር ንብረት አለዉ፡፡ ዝቅተኛው የአየር ንብረት በአማካኝ 60c ሲሆን ነገር ግን ወደ ቀይባህር በረሀ አካባቢ እስከ 600c ይደርሳል፡፡ በአብዛኛዉ የሀገሪቱ ክፍሎች በክረምት ወራት ይኸውም ሰኔ ሀምሌና ነሀሴ ውስጥ ከፍተኛ የዝናብ መጠን ይመዘገባል፡፡

ዘመን አቆጣጠር

ኢትዮጵያዉያን ከኦሪት ጀምሮ ራሳቸው የቀመሩትን የዘመን አቆጣጠር እስካሁን ድረስ ጠብቀው ይጠቀሙበታል።  በአንድ ዓመት ውስጥ አስራ-ሁለት ባለሠላሣ ቀናት እና አንድ ባለ አምስት (ስድስት  በአራት ዓመት) ቀን ወር አላት።በየአራት ዓመቱ አድ ቀን ይጨመራል። የአመተ ምህረት ዘመናት ከጎርጎርዮስ ‘አኖ ዶሚኒ’ በ7 ወይም 8 አመታት የሚለይበት ምክንያት፣ ከኢየሱስ ክርስቶስ ልደት 400 አመት ያህል በኋላ አኒያኖስ እስክንድራዊ ዘመኑን ሲቆጥረው በመጋቢት 29 1 ዓ.ም. እንደ ሆነ ስለ ገመተ ይህ ዘመን 1ኛ አመት ሆኗል። ይህ አቆጣጠር የምሥራቅ ክርስቲያን አገራት ከተቀበለ በኋላም በ443 ዓ.ም. ከሮማ ፓፓና ከምሥራቅ አቡናዎች መካከል ልዩነት ተፈጥሮአል፤ በ517 ሌላ መነኩሴ ዲዮኒሲዮስ ኤክሲጉዎስ ሌላ አቆጣጠር (አኖ ዶሚኒ) አቀረበ። በሱ ግምት ዘመኑን ከአኒያኖስ ግምት በፊት በ8 አመታት ስለ አስቀደመው የአኖ ዶሚኒ  አቆጣጠር በምዕራብ አውሮፓ የበላይኛነትን አገኘ።

የወሮች ስምና አቆጣጠር

አማርኛ

ጎርጎርዮስ

በዘመነ ዮሐንስ

መስከረም ሴፕቴምበር 11 ሴፕቴምበር 12
ጥቅምት ኦክቶበር 11 ኦክቶበር 12
ኅዳር ኖቨምበር 10 ኖቨምበር 11
ታኅሣሥ ዲሴምበር 10 ዲሴምበር 11
ጥር ጃንዋሪ 9 ጃንዋሪ 10
የካቲት ፌብርዋሪ 8 ፌብርዋሪ 9
መጋቢት ማርች 10 ማርች 10
ሚያዝያ ኤፕሪል 9 ኤፕሪል 9
ግንቦት ሜይ 9 ሜይ 9
ሰኔ ጁን 8 ጁን 8
ሐምሌ ጁላይ 8 ጁላይ 8
ነሐሴ ኦገስት 7 ኦገስት 7
ጳጉሜን ሴፕቴምበር 6 ሴፕቴምበር 6

እንቁጣጣሽ (አዲስ ዓመት)

በእንቁጣጣሽ (አዲስ ዓመት) ጊዜ እንዲህ ይባላል፣

መስከረም ሲጠባ፣ አደይ ሲፈነዳ፣
እንኳን ሰው ዘመዱን፣ይጠይቃል ባዳ።

አበባየሁወይ፤
ለምለም
ባልንጀሮቼ ቁሙ በተራ
እንጨት ሰብሬ ቤት እስክሰራ
እንኩዋን በትና የለኝም አጥር
እደጅ አድራለሁ ኮከብ ስቆጥር

አበባየሁወይ፤ (፪ ጊዜ በ አውራጇ)
ለምለም (፪ ግዜ ተቀባዮች)
አበባየሁወይ (፪ ጊዜ በ አውራጇ)
ለምለም(፪ ጊዜ በተቀባዮች)
አደይ የብር ሙዳይ፣ኮለል በይ(፪ ጊዜ በ አውራጇ)
አደይ የብር ሙዳይ፣ኮለል በይ(፪ ጊዜ በተቀባዮች)

Leave a Reply

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

Archives

Copyright and Disclaimer

Copyright © 2010 - 2015 Kefale Alemu

Copyright © [2010]. KAlemu, All Rights Reserved.