8 Responses to የዓማርኛ ለዛ

  • sewmaleta says:

    ማን ገለጸላቸዉ ይህን ሁሉ ሚስጥር?
    ማን ነግሮአቸው ነበር ነገር እንደሚያደክም
    በነጠላ ሲሆን እንደማያስደምም
    እነዲህ እንዲያወሩ
    በምሳሌ አድርገው ነገር እንዲያበራሩ
    ከመሰልቸት ይልቅ አእሚሮ እንዲፈተን
    እያሳሳቀን እያጨዋወተን
    ነገር እንዲበተን ደግሞ እንዲተነተን
    አንድ ቃል ብዙን ወክሎ እንዲናገር
    ማን አስተማራቸዉ ዪህን ሁሉ ሚስጥር?

  • Iwooket says:

    ድንቅ ግጥም ነዉ። ከምስጋና ጋር ኢሜል ይደርስወታል።

  • sewmaleta says:

    The other comment is that i dont want to scroll up to go Home page so that pls put one link on the bottom of the page.

  • demsewa says:

    ሞክሼ የአማርኛ ፊደላት እና የባለሙያዎች ማብራሪያ ክፍል አንድ
    Email ThisBlogThis!Share to TwitterShare to Facebook

    ሞክሼ የአማርኛ ፊደላት
    እና
    የባለሙያዎች ማብራሪያ
    ክፍል አንድ

    የሄኖክ ስብስብ
    ታህሳስ 2005ዓ.ም
    {PDF}
    -1-
    የፊደል ዘር ይጠበቅ ባህሉም ይከበር
    በፊታውራሪ አበበ ሥዩም ደስታ
    በፊደሎቻችን ላይ ሦስት ሀ – ሐ – ኀ፣ ሁለት አ – ዐ -፣ ሁለት ሠ – ሰ ሁለት፣ ጸ – ፀ አሉ፡፡ እነዚህ ፊደሎች የራሳቸው የሆነ የስም አጠራርም አላቸው፤ ሀሌታው ሀ፣ ሐመሩ ሐ፣ ብዙኃን ኀ፣ ንጉሡ ሠ፣ እሳቱ ሰ፣ ጸሎት ጸ፣ ፀሐዩ ፀ ይባላሉ፡፡ በጽሑፍ የሚገቡበትን ተገቢ (ተስማሚ) ቦታም አላቸው፡፡ ለምሳሌ በሁለት ፊደሎች መጠቀም ይቻላል፡፡ ሀገር አገር ይህ ትክክለኛ አጻጻፍ ሲሆን፤ ነገር ግን ከዚህ ውጪ ሐገር፣ ኀገር ብሎ መጻፍ ግን ስሕተት ይሆናል፤ የሚከተሉትን ደግሞ እንመልከት፤

    ሕገ መንግሥት፣ ሕገ ወጥ፣ ሕዝብ፣ ሕብረት፣ ዓቃቤ ሕግ፣ ወዘተ. የመሳሰሉት አጻጻፋቸው ትክክል ነው፡፡ ከዚህ ልማዳዊ አሠራር ውጪ ህገ መንግሥት፤ ህገወጥ፤ ህዝብ፤ ህብረት፤ አቃቤ ህግ ስሕተታዊ አጻጻፍ ይሆናል፤ ሌላ ማስረጃ ቢፈለግ፤ ኃይለሥላሴ የሚለው ስም ሦስት የተለያዩ ፊደሎች ይዟል፡፡ የመጀመርያው ፊደል ብዙኀን – ኃ – ሲሆን፣ ከንጉሡ -ሥ- ሳድስ፣ ከእሳቱ -ስ- ሃምስን በመጻፍ እንዲካተት ተደርጓል፡፡ ሀይለ ስላሴ ብሎ ቢጻፍ ግን የፊደሎቻችን የአጻጻፍ ሥርዓት ማፋለስ ይሆናል፤ በአቦ ሰጡኝ ፊደሎቻችን አለቦታቸው መግባትም፣ መጻፍም የለባቸውም፡፡

    በዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በማስታወቂያ ሚኒስቴር ረዳት ሚኒስትር የነበሩት የተከበሩ ብላታ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ የቅድሚያ ዓይነተኛ ሥራቸው የፊደሎች ዘሮች አለቦታቸው እንዳይጻፉ መጠበቅ ነበር፤ በዚያን ወቅት ተማሪ ሁኜ አልፎ አልፎ በጋዜጣ እንዲወጣልኝ አንድ አንድ ሐሳብ በማመንጨት እጽፍ ስለነበር ብዙ ጊዜ አርመውኛል፡፡

    ከእሳቸው በተማርኩት ትምህርትና ባገኘሁት ልምድ አእምሮዬን አሻሽያለሁ፡፡ በቀድሞው የንጉሠ ነገሥቱ ዘመነ ሥርዓት የክፍል ሹም የመጀመርያ ሹመት ሆኖ ወደ ላይ እንደሚከተለው ይዘልቃል፡፡ ዲሬክተር ዋና ዲሬክተር፤ ረዳት ሚኒስትር ምክትል ሚኒስትር፣ ሚኒስትር ዲ-ኤታ፤ ሚኒስትር፡፡ ከምክትል ሚኒስትር ወደ ላይ ያሉት እስከ ሚኒስትር ማዕረግ የደረሱት ክቡር ይባላሉ፡፡ ከዚህ በታች ያሉትን ግን ክቡር አይባሉም፡፡ በተመሳሳይ ያሉትን ማለት ኮሚሽነሮች፤ ሌ/ጀኔራሎች፣ አምባሳደሮች ክቡር ይባላሉ፡፡ ሚኒስትሮች የነበሩ በዳሬክተርና በሥራ አስኪያጅነት ሥራ ቢመደቡ እንኳን የቀድሞውን የሚኒስትር ማዕረጋቸውና ክብራቸው አይቀነስባቸውም፡፡ ክቡር መባል አለባቸው፡፡ ሥርዓት ነውና፡፡ ይህንኑ መለመድ ይገባዋል፤ በወታደሩ ሹመት አሰጣጥ ግን ያለው ሥርዓት የተጠበቀ ስለሆነ መልካም ነው እላለሁ፡፡ ከዚሁ ሌላ የምለው አለኝ፡፡ ባሁኑ በኢሕአዴግ መንግሥት ዘመን አምባሳደር ነዋሪ የማዕረግ መጠሪያ ስም ሆኖአል፡፡ አንድ አምባሳደር የዲፕሎማሲውን ሥራ አቁሞ ሲዛወር ልክ በሥራው እንዳለ ተቆጥሮ “አምባሳደር” እየተባለ መጠራት የለበትም፡፡

    ለምሳሌ በዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት አምባሳደርነት ተሹመው የነበሩት ክቡር አቶ ጋሻው ዘለቀ፣ ክቡር አቶ ዘነበ ኃይለ፣ ክቡር ልጅ መንበረ ያየህ ይራድ፤ ክቡር ፊታውራሪ መሐመድ ሲራጅ ብዙ ዘመን በአምባሳደርነት ሲሠሩ ቆይተው ተልእኮዋቸውን ፈጽመው ወደ አገራቸው ሲመለሱ አምባሳደር የሚል ቀርቶ በቀድሞ ስማቸው አቶ ተብለው ነበር የሚጠሩት፤ ይህንኑ ጠይቆ ለማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ፊታውራሪ የነበሩትም፤ ፊታውራሪ ተብለው ይጠራሉ፡፡ ዘላቂ ሆኖ ከሰው ጋር ቅጽል የማዕረግ ስም ሆኖ የሚያገለግል ነው፡፡ በራሴ ምሳሌ ልውሰድ፤ ከግርማዊ ጃንሆይ በአዋጅ የተሰጠኝ የማዕረግ ስም ፊታውራሪ ነው፤ በዚህ ምድራዊው ዓለም እስካለሁ ድረስ የምጠራበት ሲሆን፣ ከሞትኩም በኋላ እጠራበታለሁ፡፡ እንዲሁም በንጉሠ ነገሥቱ መልካም ፈቃድ የሚሰጠው የሥልጣንና ማዕረግ ተዋረድ ባላምባራስ፣ ግራዝማች፣ ቀኛዝማች ፊታውራሪ፣ ደጀዝማች፣ ቢትወደድ፣ ራስ ቢትወደድ፣ ልዑል ራስ፣ አልጋ ወራሽ፣ ንጉሥ ንጉሠ ነገሥት ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ብላታ፣ ብላቴን ጌታ፣ ፀሐፊ ትዕዛዝ፣ ሊቀ መኳስ በሕይወት ሳሉ ይጠሩበታል፡፡ ከሞቱም በኋላ ስማቸውና ታሪካቸው በተነሣ ቁጥር ከመቃብር በላይ ሆኖ በማዕረጉ ስም ይጠሩበታል፡፡

    አምባሳደር ግን የማዕረግ ስም መጠሪያ ስላልሆነ የዲፕሎማሲ ሥራቸውን ሲያቋርጡ አምባሳደር ተብለው ሊጠሩበት አይገባም፡፡ በሌላ መንግሥት የማይሠራበት ሲሆን የኢትዮጵያ መንግሥት ለብቻው በዚህ ስም አጠራር ሕጋዊ ማድረጉ ተገቢ አይመስለኝም፡፡ እንደ ማዕረግ በዘላቂነት ይጠሩበት ከተባለ እኔ ከማሳሰብ በቀር እምጎዳበት የለም፡፡ ከዚህ ጋር የማያይዘው ሌላም አለ፤ ከላይ በዝርዝር እንደገለጽኩት ባሁኑ ሰዓት ዲሬክተር ጄኔራል እየተባሉ አንዳንድ ሹማምንት ይጠሩበታል፡፡ በእኔ አስተያየት ዲሬክተር ጄኔራል ከማለት ይልቅ ዋና ዲሬክተር ቢባሉ ወይም ለስም አጠራሩ የሚቀል ስለሆነ ረዳት ሚኒስትር እየተባሉ ቢጠሩ መልካም ነው፡፡ በዚህ ቢታረም ያማረ ይሆናል፡፡

    በማጠቃለያ የማቀርበው ሐሳብ በየዕለቱ እና በየሳምንቱ በሚታተሙ ጋዜጦች መጽሔቶች፣ መጻሕፍት የፊደሎቻችን ዘሮችና ልማዳዊ የአጻጻፍ ሥርዓቶች ይጠብቁ (ይከበሩ) በማለት ሐሳቤን እቋጫለሁ፡፡ እንዲሁም የኮምፒውተር ፀሐፊዎች ይህንኑ የአጻጻፍ ስልት (ፈለግ) ተከትለው ይጠቀሙበት በማለት መልእክቴን አስተላልፋለሁ፡፡ በተጨማሪም ደራስያን፣ አስተማሪዎች፣ ማተሚያ ቤቶች፣ ከያኒያን ይህንኑ እንዲተገብሩ ማድረግ የግል ኃላፊነት ስላለባቸው ትኩረት ይስጡበት እላለሁ፡፡

    ሌላው መታረም የሚገባው፣ “ስፖርት” እየተባለ የሚጻፈው ነው፡፡ ምክንያቱም የአውሮፓ ፊደል ኤስ (S) የእ ፊደል ድምፅ ስላለው፣ Sport ቢጻፍ ትክክል ነው፤ የእኛው ፊደል (ስ) ግን ድምፁ የተዋጠ ስለሆነ እ ፊደል ተጨምሮበት “እስፖርት” ቢባል የተሻለ ነው፤ እንዲሁም ለርምጃ እርምጃ ቢባል፣ በኔ በኩል ጥሩ ስለሆነ ታስቦበት ቢታረም መልካም ይመስለኛል፡፡
    ምንጭ ሪፖርተር ጋዜጣ

    -2-
    የሐበሻ ፊደላት ለውጥ ያስፈልጋቸዋል?

    በተመስገን ታ

    በአገራችን ሚዲያዎች ፊደሎቻችን ማሻሻያ ይደረግባቸው፣ አይ አይደረግባቸውም፡፡ ማሻሻያ ማድረግ ቢያስፈልግስ መብቱ የማነው? በሚሉ ጉዳዮች ጐራ ተለይቶ ክርክሩ ጦፏል፡፡ እኔም እንደ ዜጋ ጥያቄው አጫረብኝ፡፡ የሐበሻ ፊደላት ለውጥ ያስፈልጋቸዋል? የሚል፡፡ እርግጥ ነው፡፡ የፊደላቱን ምልክት ከማወቅ ባለፈ ብዙዎቻችን የምልክት አሰያየሙን ሥረ መሠረት አናውቅም፡፡

    በዚህም የተነሣ በሞክሼ ፊደላት አጠቃቀማችን ላይ ጽሑፋችን ሁሉ ዝብርቅርቅ ነው፡፡ ይህንንም ጽሑፍ ስጽፍ ይኼው የሞክሼ ፊደላት ሰፊ አማራጭነት በሰጠኝ ነፃነት አንድን ቃል በተለያዩ የሞክሼ ፊደላት እጽፈዋለሁ፡፡ እነዚህ ሞክሼ ፊደላት እንደ አማራጭ የምንጠቀምባቸው ሰፊ ነፃነት ያጐናፀፉን አድርገን ከመውሰድ ባለፈ የትርጉም መዛባት ወይም በአጠቃቀም መዘበራረቅ ሥነ ጽሑፉን ጥላ ያጠላንበት መስሎ አይታየንም፡፡ የትርጉም መዛባት ስለማምጣት አለማምጣቱም ሆነ የተዘበራረቀ አጠቃቀማችን ችግር ያስከተለ ስለመሆኑ ፊደሎችን ለመለየት ስንማርም ሆነ ከዚያ ባለፈ ያገኘነው ተዛማጅ ትምህርት ስለሌለ ፊደሎችን በምንጠቀም ሰዎች የምንወቅስበት አንድም አግባብ የለም፡፡ ታዲያ ተወቃሹ ማን ይሁን ሲባል የፊደላቱ ባለቤት፣ ቋንቋን የሚያስተምሩና ብሔራዊ ቋንቋዬ ነው ያለው መንግሥት እንጂ፡፡

    የአማርኛ ፊደሎቻችን የራሳቸው ፊደላት ካሏቸው አገሮች ጋር በእኩል የሚመደቡን በመሆናቸው ከክብር አንፃር ክብርና ኩራት የሚያሰጡ ሲሆን፣ ከታሪክ አንፃር ደግሞ ታሪካዊ ናቸውና በቅርስነትም የሚታዩ ሊሆን ይገባል፡፡ ብዙ ጊዜ የተንጋደደ አስተያየት የምንይዝ ሰዎች ቅርስ በዩኔስኮ ዕውቅና ካላገኘ በስተቀር ቅርስነቱን ዝቅ አድርጐ ወይም አነስተኛ የቅርስነት አመለካከት እንዳለው የመገመት አባዜ ያለብን አለን፡፡ ይህ አመለካከት ሙሉ በሙሉ ከሥሩ ተነቅሎ መጥፋት ይኖርበታል፡፡

    በሌላ መልኩ ደግሞ ቀደምት አባቶች የኛ የሆኑ ፊደላትን ሲቀርፁ ከአነጋገር ጋር በተያያዘና ቃል መሥርተው በሚፈጥሩት ድምፅ አዝለውት የሚመጡት የመግባቢያ ትርጓሜ ጥልቀት ባለው መልኩ ፈትሸውት ያስቀመጡት ነውና ጥንታዊ ኢትዮጵያውያን ፈላስፎቻችንን የምናደንቅበትና ክብር የምንሰጥበት ቅርሶች ናቸው፡፡ በእርግጥ ቁጥሮቻችንና ፊደሎቻችንን የፈለሰፉ ኢትዮጵያ ፈላስፎቻችን የፈጠሩትን ፊደል ተጠቅመው እራሳቸውን እነማን እንደነበሩ እንደ አውሮፓውያኑ፣ ላቲኖቹ፣ እስያውያኑ፣ ወዘተ መዝግበው ለትውልድ ባለማስተላለፋቸው በስማቸው እያነሳን ስናሞግሳቸው እንዳንኖር ሆነዋል፡፡ ዳሩ ግን በአገራችን እንደቱፊት ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃልም አለ፡፡ ‘ስለ አንተ ምላስህ ሳትሆን ሥራህ ይመስክር’ የሚለው የአገራችን ሃይማኖታዊ ቱፊቶች እንደነበሩ ተጠብቀው በቅብብሎሽ አሁን ላይ በመድረሳቸው በእምነቱም ቢሆን ከዓለም ሃይማኖቶች በተለይም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልዩ ሆነን እዚህ ጊዜ ላይ ደርሰናል፡፡ ነብዩ ሙሴ የተወለደባት ግብፅ እንዲሁም ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደባት እሥራኤል ያልጠበቁትን ሃይማኖታዊ ቱፊት ኢትዮጵያ ውስጥ ተጠብቆ ከልጅ ልጅ እየተሸጋገረ አሁን ካለንበት ደርሷል፡፡

    ምናልባትም ፊደሎቻችንን የፈጠሩትም ይሁኑ በተለያዩ ጊዜያት ያሻሻሉትም ጭምር በዚሁ መንሳዊ ቱፊት መነሻነት ሊሆን ይችላል፡፡ ስማቸው በክብር ተመዝግቦ ለትውልድ ያልተሸጋገረው፡፡

    በሌላ መልኩ ደግሞ እነዚሀን ፊደላት የፈለሰፉ ፈላስፎቻችን ስማቸውን በክብር መዝገብ ያኖሩ ቢሆንም ይህ የክብር መዝገብ በአግባቡ ለትውልድ እንዲተላለፍ ሆኖ ባለመቀመጡ ምክንያት በመጥፋቱ ወይም በመበላሸቱ ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚህ ባለፈ ደግሞ የሥነ ጽሑፍ ቅርሶች እስካሁን የሚሰበሰቡት በቤተ ክርስቲያን በመሆናቸው ቤት ክርስቲያኖቻችንን ባለቡት ሁሉ የማወቅና በሙዚየምነት የያዟቸውን የሥነ ጽሑፍ ቅርሶች በዝርዝር አለመታወቁ ምክንያት ወደ ሕዝብ እውቀት ስላልመጡ ሊሆን ይችላል፡፡

    አገራችን በተለያዩ ጊዜያት በውጭ አገሮች ስውርና ቀጥተኛ የታሪክ መዛግብትን ዝርፊያና ድምጥማጣቸውን የማጥፋት ሴራ እንዲሁም በአገር ውስጥም ቢሆን በየጊዜው ይካሔድ በነበረው የእርስ በእርስ ጦርነት ምክንያት ከግንዛቤ ማነስ የቤተ መዘክር ታሪኮቻችን ይወድሙ እንደነበር በአፈታሪክም ቢሆን የሚነገሩ አሉ፡፡ እናም በነዚህ ሁኔታዎች የነዚህ የፈላስፎቻችን ታሪክ ጠፍተው ሊሆን ይችላል፡፡ ታዲያ የቤተ ክህነትን ዜማና አቋቋም የፈለሰፈው ቅዱስ ያሬድ ታሪክ እዚህኛው ትውልድ የደረሰው ታሪኩ ተመዝግቦ ሳይጠፋ ከትውልድ ወደ ትውልድ በመተላለፉ ነው፡፡ በመሆኑም ቁጥሮቻችንና ፊደሎቻችንን የፈጠሩትም ሆኑ ያሻሻሉት ፈላስፎች ለምን በስም ሊታወቁ አልቻሉም?

    በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ወይም ትክክለኛ ባልሆነ የውጭ የተሳሳተ አስተሳሰብ ተፅዕኖ ታሪክን ወደ ውጮች ለመወርወር የሚታሰብበት አጋጣሚ ይታያል፡፡ ይህም በመሆኑ የኛነት መገለጫ የሆኑትን ፊደላትም የውጭ አስተዋጽኦ ሊኖራቸው ይችላል ብለን የምናስብ ኢትዮጵያዊ ትውልዶች እንዳንኖር እሰጋለሁ፡፡ ከድምፅ አወጣጥ ጋር አስተሳስሮ ለሚፈጠረው ድምፅ ምን ዓይነት የፊደል ምልክት ይኑረው ብሎ በማሰብ ምልክቱን ማስቀመጥ ቋንቋው የአፍ መፍቻው ካልሆነ እንዴት አስቸጋሪ እንደሚሆን ምንም ሌላ ማረጋገጫ የለውም፤ በአፍ መፍቻ ቋንቋችን በየራሳችን የምናውቀው ነውና፡፡ ለምሳሌ ያህል በጥቂቱ ለመጥቀስ የኦሮምኛው፣ የአማርኛውና የወላይተኛው የአነጋገር ዘይቤ ልዩነቶችን በተወሰኑት ቃላት መጥቀስ ይቻላል፡፡ የትግርኛ ቋንቋ በትናጋ የሚናገረውን አማርኛው በከንፈሩ ሊናገረው ይችላል፡፡ በኦሮምኛ ላልቶ የሚነገረው በአማርኛው ከሮና ጠንክሮ በማጥበቅ ሊነገር ይችላል፡፡ በወላይተኛው ቃሉ የሌለ ይሆንና ሊጣመም ይችላል፡፡ ለአብነት ያክል ቢዳዳ፣ መቀሌ፣ ፈረስ፣ ወዘተ መጥቀስ ይቻላል፡፡ ስለሆነም ከነዚህ እውነታዎች መነሻነት የአማርኛ ፊደሎቻችንን የፈለሰፉ ፈላስፎች ወይም ያሻሻሉት ሰዎች ቋንቋው የአፍ መፍቻቸው ሊሆን እንደሚችል በዋናነት መገመት ይቻላል፡፡

    የሐበሻ ፊደላትንና ቁጥራትን እነማን ፈጠሯቸው? የሚለውን ጥያቄ ብቻ ሳይሆን እንዴት እንደምንጠቀምባቸውም መግለጫ ወይም አንድምታ አብሮ ለትውልድ ባለመተላለፉ አሁነኛው ትውልድ ላይ ግር የማለት ሁኔታ እየታየ ነው፡፡ እያንዳንዱ ፊደል ተጣምሮ ከሚሰጠው ትርጓሜ አንፃር የድምፅም ሆነ የፊደሉ ተጠሪነት የየራሳቸው አግባብነት አላቸው፡፡ እነዚህን የፊደል አግባብነትና የሚወክሉትን ድምፅ ጭምር እንዴት? መቼ? እና ለምን? መጠቀም እንዳለብን የፊደላት አጠቃቀም አንድምታ ሊገኝ አልቻለም፡፡ ይህም በመሆኑ ሞክሼ ፊደላትም ሆኑ በአንድ ፊደል ስረ ግንድ የሚነበቡ ተመሳሳይ ድምፆች የፊደሎቹ ዘሮች ያለአስፈላጊ እየመሰሉ የመታየት እንዲሁም መሻሻል አለባቸው የሚል አስተሳሰብ እየገነነ እየመጣ ነው፡፡ ለማጥፋትም የሚያኮበኩቡ ከዚህም ባለፈ የሚዝቱ ‹‹ምሁራን›› እየታዩ ነው፡፡ ምሁር ማለት ፈላስፋ ማለት አይደለምና ግራ ቢገባቸው አይገርምም፡፡ ብዙዎቻችን ለያዝነው የትምህርት ደረጃ በተሰጠን የዕውቅና ወረቀት ላይ ብቻ ተንጠላጥለን ሥራችን ሳይሆን ልባችን በትቢት ይወጠራልና፡፡ በአንድ ወቅት አንድ ሥልጠና ላይ አሠልጣኙ የንድፈ ሐሳባውያንን ቱሩፋት እንዲህ በማለት ነገረን፡፡ ‹‹አንድ ወላጅ ልጃቸው ሁልጊዜ ፈተና ይደፍናል፡፡

    ሁሌም አንደኛ ይወጣል፡፡ በዚህ ችሎታው የሚደሰት ልጅ ፈተና የመድፈኑንና አንደኛ የመውጣቱን ዜና ለአባቱ ሲናገር አባት አይሞቃቸውም ወይም አይበርዳቸውም፡፡ የሚደሰቱም የሚከፉም አይሆኑም፡፡ ልጅ ታዲያ የሚጠብቀው የአባቱን እጅግ አድርጐ መደሰት ነበርና ‘አባዬ ጉብዝናዬን እያየህ ለምን እጅጉን ደስ አላለህም?’ ይልና አባቱን ይጠይቃል፡፡ አባቱም በምላሹ ልጄ ሆይ ጐበዝ ነኝ የምትለኝ እኮ መምህሮችህ የነገሩህን ሁሉ በፈተናቸው መልሰህ ስለነገርካቸው ነው፡፡ እኔ ግን በጉብዝናህ የምደሰተው አዲስ ነገር ስትፈጥር ነው አሉት፡፡››

    ፈላስፋ ሳይኮን ለመሆን የነበረን አጥፍቶ በዘፈቀደ አዲስ ተካን ማለት ግን ‘ምሁር’ የሚለውንም ማዕረግ ዝቅ እንዳያደርገው እሰጋለሁ፡፡ ያም ሆነ ይህ በፊደሎቻችን አጠቃቀም ግራ መጋባት የሁለችንም ችግር ነው፡፡ ፊደላትን ያለቦታቸው እየደነቀርናቸው ለማስተላለፍ የተፈለገው መልዕክት በስህተት ሌላ ትርጓሜ ሊይዝ እንደሚችል ይገመታል፡፡ በዚህ ሰበብም ሥነ ጽሑፎቻችን የተዛቡ እንዳይሆኑ ስጋቱ አብሮ አለ፡፡ ከዚህም ውጭ የፊደላት አጠቃቀማችን ሥርዓት ያለው ሳይሆን በዘፈቀደ በመሆኑ የምርጫ ነፃነት ቢኖረንም ዳሩ ግን የአተረጓጐም ለውጡ በቀጣይ ትውልድ ችግር እንዳያመጣ ያሰጋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ለለማጆችም ተጋኖ እንደሚቀርበው ባይሆንም በተወሰነ ደረጃ ግራ ሊያጋቡ ይችላሉ፡፡

    ቁጥሮቻችንም ቢሆኑ በሂንዱ ዓረቢክ ቁጥሮች ቁጥጥር ሥር በመዋላቸው በመቀበሪያ ጉድጓዳቸው ጫፍ ላይ ነው ያሉት፡፡ በአገራችን ቀን መቁጠሪያዎችና በቤተ ክህነት ካልሆነ በስተቀር በየትኛውም የሒሳብ ስሌት ውስጥ ገብተው ትውልድ እንዲጠቀምባቸው አልተደረገም፡፡ የስሌቱ ይቅርና ሺዎችን ቁጥሮች ወክሎ ለመጻፍ ግርታ ተፈጥሯል፡፡ የሐበሻ ቁጥሮች መሠረታዊ ምልክታቸው እስከ መቶ ብቻ በመሆኑ ከመቶ በላይ እንዴት እንደምንጠቀምባቸው የተቀመጠ ባለመኖሩ፡፡ ለዚህም እንደ አስረጂነት በእኛው የዘመን አቆጣጠር የሁለት ሺሕ ዓመተ ምሕረትን ማንሳት ይቻላል፡፡ በጊዜ መቁጠሪያ (ካላንደሮች) ላይ በዚህ ጊዜ የተጻፉትን ብናይ በቤተ ክህነት ጭምር በተለያዩ የግልና የመንግሥት መሥርያ ቤቶች የተለያዩ ነበሩ፡፡ ምንም እንኳን የመረጃ ሥነ መሠረቶች ወይም በጥናት የተደረሰባቸው የመግባቢያ መረጃዎች ባይኖሩም ልብ ለልብ በመተዋወቅ ወደ አንድ ወጥ የተመጣ ሆነ እንጂ፡፡

    በቁጥሮቻችንም ሆነ በፊደሎቻችን ሌላው የራሳችን የኢትዮጵያውያን ችግር ደግሞ የኛ ካልሆኑት የውጭ የቁጥርና የፊደላት ምልክቶች ጋር እናነፃፀርና የኛ የሆነውን የኛነት መኩሪያችንን ሽርሽርን ለውጬ ተፅዕኖ እጅ እንሰጣለን፡፡ የኛ የሆኑትን በጥልቀት እንዲጠኑ በማድረግ ከጊዜ ለውጥ ጋር ከፍተቶች ታይተውባቸው ከሆነ ክፍተታቸውን ከመሙላት ይልቅ ተወቃሽ በማድረግ ከታሪክ ማኅደር እንዲነሱ ቢጫ ማስጠንቀቂያ እናሳያለን፡፡ የውጩ ተፅዕኖ ያደረገብን መሆኑን አዙረን ልናይ ባለመቻላችን ከዘመኑ ኪነ ብጀታ (ቴክኖሎጂ) ጋር የማይጓዙ ብለን በሐሰት መረጃ ወንጀለኛ እናደርጋቸዋለን፡፡ የኛ የታሪክና የቅርስ መገለጫ የሆኑንን የቁጥርና ፊደላት ምልክቶቻችን ከላይ እንደገለጽኩት ከመኮነን ባለፈ እንዴት እናበልጽጋቸው? ሳይሆን የሐሰት መረጃን መሠረት አድርገን እንዴት እናጥፋቸው? የማለት ያህል ይሆንብኛል፡፡

    በእኛው በአገራችን እንኳን ብንወስድ የአሁኑ መቀምር (ኮምፒውተር) መተየቢየን (ታይፕራይተርን) ቦታ ከመረከቡ በፊት ከቁም ወይም የብራና ጽሑፍ ወደ መተየቢያ ነበር የተሸጋገርነው፡፡ ኦሎምፒያ መተየቢያን ወደ ገበያ ሲያወጣ ይህ የመጻፊያ መሣርያ ለትንግርት ተደንቋል፡፡ በወቅቱ ዋጋውም ሰማይ የነካ እንደነበር ታሪክ ዘክሮታል፡፡ ዳሩ ግን የኛውን የፊደላትና የቁጥር ምልክቶች አያውቅም ነበር፡፡ ይህ መተየቢያ የኛነት መገለጫ የሆኑትን ቅርሶቻችንን ፊደላትንና ቁጥሮችን በቅኝ ገዥነት ሊያደክም ለወረራ የመጣ መሆኑን የተገነዘቡ የጊዜው አገር ወዳድ ባለሙያ ኢንጂነር ተረፈ ራስወርቅ ዝም ብለው ማየት ህሊናቸው አልቀፈደላቸውም፡፡ ወረራውን በፀረ ወረራ ትግል ጀመሩ፡፡

    ኢንጂነር ተረፈ ራስወርቅ ለሰላማዊ ትግላቸው ኦሎምፒያ ኦሊቬቲ ወደሚገኝበት አሜሪካ ተጉዘው የመጀመርያ የሰላም ጥይታቸውን ለኦሎምፒያ ኦሊቬቲ ተኮሱ፡፡ ይኸው ኩባንያ የኢትዮጵያን ፊደላት የሚያስተናግድ መተየቢያ እንዲያመርት ኢንጂነሩ ሲጠይቁ ልክ አሁን እንደሚባለው የተሰጣቸው የኢትዮጵያ ፊደላት ቁጥር ሁለት መቶ ሰባ በመሆኑ እጅግ የበዛ ባሕርያት (ካራክተር) አላቸው፡፡ ስለሆነም የሐበሻን ፊደላትና ቁጥሮች የያዘ መተየቢያ ላመርት አልችልም ነበር ምላሹ፡፡ እዚህ ላይ ልብ ልንለው የሚገባ ጉዳይ አለ፡፡ ብዙ የሆነን ነገር ማስተናገድ ትንንሾች ሲመጡ ሰፊ አማራጭ ይዞ ከመገኘት አንፃር ትንንሾችንም ማስተናገድ ቀላል ይሆናል፡፡ ግን ኦሎምፒያ ኦሊቬቲ አላደረገውም፡፡

    ኢንጂነር ተረፈን ምላሹ እጅ እንዲሰጡ ወይም ከጦርነቱ እንዲሸሹ ወይም እንዲያፈገፍጉ አላደረጋቸውም፡፡ አፄ ምኒልክ ዓድዋ ላይ ጣሊያንን ድል ለማድረግ ከእቴጌ ጣይቱና የጦር ባልደረቦቻቸው ጋር ሆነው ስልት እንደነደፉት ሁሉ ኢንጂነር ተረፈም ድል የማድረጊያ ስልት ማሰላሰል ጀመሩ፡፡ ስልቱንም አገኙት፡፡ የጦርነት ስልት ለጦርነት የሚሆን ሲሆን የንግድ ስልት ደግሞ በንግዱ አካሔድ መሆን እንዳለበት ተረዱት፡፡ አደረጉትም፡፡ ኦሎምፒያ ኦሊቬቲን በንግድ የሚቀናቀነው ማነው? የሚለውን ምላሽ ማግኘት ነበር፡፡ አገኙም፡፡ ተቀናቃኙ የጀርመኑ ሲሜንሶ መሆኑን፡፡ ኢንጂነር ተረፈም የአገራቸውን ፊደል ከወረራ ለማዳን እ.ኤ.አ በ1960ዎቹ ወደ ጀርመኑ ሲሜንሶ ተጓዙ፡፡ ከቦታውም ደረሱ፡፡ ልክ እንደ ኦሎምፒያ ኩባንያ እንዳቀረቡት ሁሉ ለሲሜንስም የኢትዮጵያ ፊደል የያዘ መተየቢያ ሠርቶ እንዲያወጣላቸው ጥያቄ አቀረቡ፡፡ ሲሜንስም ጥያቄያቸውን ተቀበላቸው፡፡ የኢትዮጵያ ፊደላትን የያዘውን መተየቢያ ከነፈጠራ ባለቤትነት ሠርቶ አስረከባቸው፡፡

    በቁጥርና ፊደል መተየቢያነት ከመቶ ዓመታት በላይ በዓለማችን ሪከርድ ያለው ይኸው መሣርያ አገልግሎቱን ለመቀምር (ኮምፒውተር) እስካስረከበበት ጊዜ ድረስ በታማኝነት የኢትዮጵያን ፊደላትና ቁጥሮች ተንከባክቦ በመያዝ ዘመን ላመጣው መቀምር አስረከበ፡፡ የዘመኑ መቀምር እንደቀድሞው ኦሎምፒያ ኦሊቬቲ የአማርኛ ፊደላት ብዙ በመሆናቸው ላስተናግዳቸው አልችልም አላለም፡፡ ያለምንም ችግር እንዳሉ ተረክቧቸዋል፡፡ ተረክቦም በማገልገል ላይ ነው፡፡

    የኛዎቹ ‹‹ምሁራን›› የፊደሎቻችን አስቸጋሪነት ልክ እንደ ኦሎምፒያው ኦሊቬቲ እየሆኑብን ነው፡፡ ኪነ ብጀታው (ቴክኖሎጂው) ወደ ወለደው መሣርያ እንዴት እናሳድገው ወይም እኛው እራሳችን የኛኑ ቅርሶች ሊያሳድግ በሚችል መልኩ አዲስ ኪነብጀታ እንፍጠር ሳይሆን ሌሎች የፈጠሩትን ኪነብጀታ ተረክበን የኛነት መገለጫ የሆኑንን የቁጥርና የፊደል ቅርሶቻችንን ልናጠፋ ወይም ልናደበዝዝ ላይ ታች እንታክታለን፡፡ የውጮች ኪነብጀታ የኛን ያስቸግረዋልና እናጥፋቸው ወይም እናዛባቸው በሚልም ዱለት መዶለት ጀምረዋል፡፡ መዶለቱ ከኢንተርናሽናል ፎኔቲክ አሶሴሽን (International Phonetic Association (IPA)) ጋር ከሆነ ይህንን በሌላ መስመር ማስተናገድ ነው፡፡ እኛ እኛን ከሆን መፍጨርጨር ይኖርብናል? ወይስ ሌሎችን ለመምሰል ታሪኮችንን ማጥፋት?

    ዛሬ በሥነ ጽሑፍ ታሪክ ስናዛባ ነገ ደግሞ ቁሳዊ የሆኑ የታሪክና የሥልጣኔ አሻራዎቻችን የሆኑትን ቁሳዊ መገለጫዎቻችን አክሱም፣ ላሊበላ፣ ፋሲለደስ፣ የጀጐል ግንብ፣ ወዘተ ከቻለ ይኸው ትውልድ ካልሆነም ቀጣይ ትውልድ እንዲያጠፋቸው እያመቻቸን መሆናችንን የምንረዳ ስንቶች ኢትዮጵያውያን አለን? ምናልባትም የቁጥርና የፊደሎቻችንን ምልክት የፈጠሩትን ፈላስፎች ዝክረ መዝገብ ለትውልድ ተላልፎ እንዲታወቁ ያልሆኑት በዚሁ ሁኔታ ጠፍቶስ ቢሆን? አይሆንም አይባልም ሆኖ ይሆናል፡፡

    በጣም የሚያስገርመኝ ደግሞ የቁጥሮችም ሆነ የፊደላቱ ባለመብት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሆና እያለ በግብታዊነት እናሻሽል ብሎ መነሳሳቱ አስገርሞት ይፈጥራል፡፡ እዚህ ላይ እናሻሽል ብለው የተነሱት ብቻ አይደሉም አስገራሚዎች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንም ብትሆን የቁጥሮችንም ሆነ ፊደላቱን ቱፊታዊ አመጣጥ፣ አጠቃቀምና አንድምታዎች ከጊዜያቱ ጋር በተጣጣመ መልኩ እንዲታወቁ እናም ጉድለትም ካለባቸው መሠረታቸውን ሳይለቁ ጥናትን መሠረት በማድረግ ክፍተታቸው እንዲሞላ አለማድረጋቸው ነው፡፡ ሌላው ይቅርና የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል አይቀየርም፡፡ የሚያስተላልፈውም መልዕክት እንዲሁ፡፡

    ነገር ግን እንደየትውልዱ አረዳድና የቋንቋ አጠቃቀም በሊቃውንት ጉባኤ በተወሰነ ጊዜ ይሻሻላል፡፡ ፊደሎቻችንና ቁጥሮቻችንስ እንዲሁ ቢሆኑ ምን ይል ነበር? በዚሁ የፊደሎቻችን ይሻሻሉ የምሁራን ጉባኤ ላይ ዛሬ በሕይወት የሌሉቱ ነፍሳቸውን ይማርና እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሠዓሊ አፈወርቅ ተክሌ ተጋባዥ ሆነው ቀርበው ስለነበር ጉባኤው የኃጢአት ምስክርነት እስከሚመስላቸው ሰቅጥጧቸው ተነስተው የተናገሩት እንደሚከተሉት እምነት የይሻሻሉ አቅራቢዎችን ‹‹ገዥቻችኋለሁ›› ነበር ያሉት፡፡ ለትውልዱም አደራ ያስተላለፉት ይኸንኑ የጥፋት መልዕክት እንዳይቀበል ነበር፡፡ እሳቸውም ቢሆኑ ሐሳባቸውን ያስተላለፉት ፊደሎቻችን ምንም እንከን የለባቸውም ብለው አቋም በመያዝ አልነበረም፡፡ ጉድለት ቢኖር እንኳን በጥልቀት እየተጠና መሠረቱን፣ ታሪካዊነቱንና ቅርስነቱን ሳይለቅ ወይም ሳይዛባ እንዲደፈን እንጂ፡፡

    የሐበሻ ፊደሎቻችንና ቁጥሮቻችን ለዚህ ዘመን አጠቃቀምና ላለፉት ዘመናትም አስቀምጠውት እዚህ የደረሱበት ፋይዳና ያበረከቱት ድርሳናትን ጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ ለማሻገር ያሉባቸው ችግሮች ሊጠኑ ይገባል፡፡ ያሉባቸው ችግሮች ብቻ ሳይሆኑ አዎንታዊ ጐኖችም እንዲሁ፡፡ በመጀመርያ ሲፈጠሩ መሠረታቸው ምን ነበር? አሁን ላይስ እንዴት እየተገለገልንባቸው ነው? ወደፊትስ በምን ሁኔታ ለትውልድ እንዲተላለፉ ይደረጋል? የሚሉና ሌሎች መሠረታዊ ጥያቄዎችን ለመመለስ ጥልቅ ጥናት ማድረጉ አስፈላጊ ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት ሞክሼ ፊደላትም ሆኑ በአንድ ሥረ ግንድ ፊደል ከግእዙ እስከ ሳብዑ ባሉ ፊደላት መካከል ቅርፃቸው የተለያዩ ሆነው የሚሰጡት ድምፅ ግን ተመሳሳይ ነው፡፡ ለምሳሌ የግእዝ ፊደላት ሀ፣ ሐ፣ ኀ፣ አ፣ ዐ ከራብዑ ሥረ ግንድ ፈደላቸው ጋር ማለትም ሃ፣ ሓ፣ ኃ፣ ዓ ተመሳሳይነት ያላቸው ይመስላል፡፡ እንዲሁም በግእዝ ላይ ያሉት ከሣልስ ፊደላት ከራብዕ ፊደላት ወዘተ ጋር በድምፅ የሚመሳሰሉ የሚመስሉ አሉ፡፡ በእርግጥ ተመሳስለው ነው? የሚመሳሰሉም ስለሚመስሉን የተመቹንን ፊደላት በሥነ ጽሑፋችን እንጠቀምባቸዋለን ትክክል ነን? በምርጫስ መጠቀም ይኖርብናል?

    ድምፃቸው ተመሳሳይ እየመሰለን ቅርፃቸውን እስከመርሳት የሚደርሱ ፊደላትም አሉ፡፡ ምሳሌ የ‘የ’ ሥረ ግንድ የሆነው ሣልሱ ‹‹ዪ›› እና ሳድሱ ‹‹ይ›› እንዲሁም ዲቃላ ፊደሎች፡፡ ይህ ለምን ሆነ? ስንል ምናልባት በአነጋገር ዘይቤ (የአክሰንት)ለውጥ የፊደሎች ድምፅ ወደ ተመሳሳይነት ድምፅ ቀርበው ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ምንን አስከተለ? ፊደላትን ተመሳሳይ ድምፅ ያላቸው ከመሰለን በዘፈቀደ መጠቀምን፡፡ ለምን በዘፈቀደ መጠቀምን መረጥን? በመጀመርያ ብዙ አማራጭ በመኖሩ የመምረጥ ነፃነትን ከመፈለግ፡፡ በሁለተኛ ደረጃ በአጻጻፍ ከሌሎች ጋር በመቀራረባቸው ግርታ እንዳይፈጠር ለየት ያለውን ለመጠቀም ከመፈለግ፡፡ በተለይ ለጀማሪዎችና በእጅ ለሚጽፉ ጽሑፎች፡፡ ምሳሌ እሳቱ ‹‹ሰ›› ከ ‹‹ለ›› ጋር በምስልነት የተቀራረቡ ስለሚመስሉ እሳቱ ‹‹ሰ››ን ከመጠቀም ይልቅ ንጉሡ ‹‹ሠ››ን የመምረጥ አንፃር፡፡ በአራተኛ አውቀነውም ይሁን ሳናውቀው ከአስተሳሰባችን ጋር የተዋሐደውን የመምረጥ፡፡ እነዚህ ምርጫዎች ምን ችግር አመጡ? በጥልቀት መጠናት የሚገባው ይሆናል፡፡

    የሰው ልጅ አመለካከቱን ቀድሞ የሚወስነው በአስተሳሰቡ የሚያሠርፀው ሥነ ልቦናዊ ምልከታውን ነው፡፡ ጐበዝ፣ ጐበዝ፣ ጐበዝ፣ . . . እየተባለ ያደገ ሕፃን በዋናነት ጐበዝ እንደሚሆንና ሰነፍ፣ ሰነፍ፣ ሰነፍ፣ . . . እየተባለ ያደገውም እንደዚሁ ስንፍናውን ተቀብሎ ተዋሕዶት የሚኖረው፡፡ የሁለቱም ተቃራኒ አስተሳሰቦች በሰዎች አስተሳሰብ ሲየርፁ የሚኖራቸው የሥነ ልቦና ተፅእኖ አላቸውና፡፡ እንደዚሁም አዎንታዊና አሉታዊ አስተሳሰብ የሚቆጣጠራቸው ሰዎች አሉ፡፡ ኦፕቲሚስትና ፔሲሚስት (Optimist and Pesmist) እንደሚባለው ማለት ነው፡፡ አንዳንዶች በጎ ነገርን በመፈለግ ለማግኘት ይታክታሉ፡፡ በሒደት በጎ ያልሆነውን ቢገጥማቸው እንኳን በጎ አለመሆኑን ማጋነን ሳይሆን እንዴት በጎ ሊሆን እንደሚችል መፍትሔ ይሰጣሉ እንጂ፡፡ በሌላ ጽንፍ ደግሞ በጎ ያልሆነውን ችግር ችግሩን ለማግኘት ብቻና ይህንኑ አጉልቶ በማውጣት አጋኖ ለማጥላላት ሲባዝኑ ይታያሉ፡፡ እርካታውም ደስታውም በጎ ያልሆነውን ማግኘት ላይ ነውና፡፡ ይኸም አያስደንቅም የሰው ባሕሪ ነውና፡፡

    መሬትና ከባቢ አየርም የተፈጠሩት ሁለቱንም ዓይነት ባህሪያትን ለመሸከም ነውና፡፡ በመሆኑም አንዱ ሌላውን ለመቀበል ወይም ለማጥፋት ማሰብ ግን የለብንም፡፡ ያም ሆነ ይህ ወደ ጀመርነው ርእስ እንመለስና የኛዎች የፊደል ጉድለት ‹‹ተቆርቋሪ ነን›› ባዮች ችግር ችግሩን ብቻ ለቅመው አጉልቶ በማሳየት የክተት አዋጅ እንዳያውጁ እነሱንም ጭምር በጥንታዊ ፈላስፎቻችንና በእነሱም ፈጣሪ ስም በጐውንም ያሳያቸው ለማለት እንጂ፡፡ በእርግጥ ‹‹ካልተበጠበጠ አይጠራም፣ በሽታውን ያልተናገረ መድኃኒት አያገኝም፣ ወዘተ›› የሚሉ መልዕክት አዘል ቱፊታዊ አባባሎች አሉን፡፡ ወደዚህኛው የፊደሎቻችን እንከን ላይ ስንመልሰው የፊደሎቻችንን ጉድለቶች ነቅሰው ማውጣታቸው ይበል፣ እሰየው፣ አበጃችሁ፣ ወዘተ ሊባሉ ይገባል፡፡ ይኸም በጉዳያዊ ጥናት (Case Studies) ሆኖ ለቀጣይ ጥልቅ ጥናቶች እንደ መነሻ መሆን ሲችል ነው፡፡ ነገር ግን ሮጦ ወደ ድምዳሜ መሔድ ግን ትዝብትም ብስጭትም ስለሚሆን ነው ጠንከር ያለ አስተያየት የተሰጠበት፡፡ አንዳንዴ እኛ ኢትዮጵያውያን የሚጐዳንን ችግራችንን በቅንነት ሲነገረንም እንደ ድፍረት የምንቆጥርና እምቧ ከረዩ የምንል ብዙ ነን እና፡፡ የሰላ ሒስ ወደ ጥልቅ ዕውቀት መውሰጃ ጎዳና መሆኑንም እንረዳው፡፡ ስለሆነም ይህ ጽሑፍ በዚህ አስተሳሰብ ተቃኝቶ የቀረበ እንጂ አዲስ ነገር ለማግኘት ምሁራዊ ትጋትን የሚከውኑ ወገኖቻችንን ለማስቀየም እንዳልሆነ ልብ ሊባል ይገባል፡፡

    ምንጭ፤ሪፖረተር ጋዜጣ

    -3-
    የሀገር ውስጥ ምሁራን በፊደሎቻችን ላይ የሚያነሧቸው ጥያቄዎችና መልሶቻቸው
    በአምሳሉ አርጋው

    የሀገር ውስጥ ምሁራን በፊደሎቻችን ላይ ብዙ ዓይነት ቅሬታዎችንና ጥያቄዎችን ሲያነሡ ቆይተዋል፡፡ አሁንም በየብዙኃን መገናኛው ማለትም በየነጋሪተ ወጉ (Radio) በየምርአየኩነቱ (Television) እና በየ መጣጥፉ በማንሣት ላይ ይገኛሉ፡፡ ለውጦችንም ማድረግ ይፈልጋሉ፡፡ ለዚህም እንዲመቻቸው ይመስላል የፊደሎቻችን ባለቤት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን መሆኑን ልቦናቸው እያወቀ እንደፈለጉ ያለከልካይ እና ጠያቂ ለውጥ ለማድረግ እንዲመቻቸው ከፊደላቱ ባለቤት ከኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ተቃውሞ እንዳይነሣባቸው የፊደላቱን ባለቤት ለባዕድ ይሰጡታል ወይም የደቡብ ዓረቢያ ነው ብለው ይሰብካሉ፡፡ 100 ዓመት ከሚጠጋ ጊዜ ጀምሮ ምሁራኑ በፊደሎቻችን ላይ ጥያቄ ሲያነሡ ቆይተዋል፡፡ የቀድሞዎቹ በተለየ ያነሡት የነበረ ጥያቄ እንደዛሬው መቀምር (Computer) ባልነበረበት ሰዓት የአማርኛ መጻፊያ መሣሪያ (typewriter) ለማሠራት የአማርኛ ፊደሎች በጣም ብዙ በመሆናቸው በሚል ሰበብ በእነሱ አባባል አላስፈላጊ ናቸው ያሏቸውን በርካታ ፊደላት ማስወገድ ወይም መቀነስ ግዴታ ነው ብለው ይከራከሩ ነበር፡፡ ነገር ግን የፊደላቱ መበርከት ታይፕራይተሩን ከመሠራት ሳያግደውና አማርኛን በታይፕራይተር መጻፍ እውን መሆን እንዳይችል ሳያደርገው ሁሉንም ፊደላት ባካተተ መልኩ ተሠርቶ በመምጣቱ በዚህ ምክንያት ተነሥቶ የነበረው የጦፈ ክርክር ለመዘጋት ቻለ፡፡

    በጣም የሚያሳዝነውና እጅግ የሚገርመው ደግሞ ጥቂቶቹ ዚኖሜኒክ ምሁራን በገዛ ፊደሎቻችን መጠቀማችን ለዕድገት እንቅፋት ሆኖናል፡፡ መጠቀም ያለብን በላቲኑ ነው ይህን ብናደርግ ዕድገት እናመጣለን የሚሉ መገኘታቸው ነበር፡፡ በራሳችን ፊደላት መጠቀማችን እንዴት ሆኖ ለዕድገት እንቅፋት ሊሆን እንደሚችል ግን አሳማኝ አይደለም፡፡ እንዲያው የሚመስል እንኳን ማስረጃ አመክንዮ ወይም ሎጂክ ማቅረብ አልቻሉም ነበር፡፡ እግዚአብሔር መቼም በየዘመኑ ሰው አያሳጣምና በአንዳንድ ልበ ብርሃን ምሁራን በእነ አብዬ መንግሥቱ ለማ የማያዳግም ምላሽ ማለትም የራሷን ፊደል ጥላ በምዕራባውያኑ እየተጠቀመች ያለችውን ቱርክን የትም አለመድረስ የራሷን ፊደል መጠቀሟ ከዕድገት ያልተገታችውንና አስደናቂ ስኬት ያስመዘገበችውን ጃፓንንና የደረሰችበትን የስኬት ወይም የዕድገት ደረጃ በማንሣት በራስ ፊደላት መጠቀም ሊያግዝ ወይም ሊረዳ ቢችል እንጂ እንቅፋት ሊሆን እንደማይችልና መረጃም ሊቀርብበት እንዳልቻለ ወይም እንደሌለ በማሳየትና በመርታት ፊደሎቻችንን ሊታደጓቸው ችለዋል፡፡

    ነገር ግን ሌሎች ያኔም ሲነሡ የነበሩ አሁንም እየተነሡ ያሉ ጥያቄዎች አሉ፡፡ ጥያቄዎቻቸውን ከመቶ ዓመታት ጀምሮ እስከ ዛሬ የሚያነሡትና በቂ መልስ ያልተሰጣቸውም አንዱና ዋነኛው ምክንያት መልስ ሊሰጡ የሚገባቸው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምሁራኑ ጥያቄዎችን የሚያነሡት ባልገባቸው ነገር ላይ በመሆኑ ጥያቄዎቻቸው የትም የማያደርሳቸው መሆናቸውን በማየት ተገቢውን ምላሽ ሳይሰጧቸው ቆይተዋል፡፡ አሁን ግን እነዚህ ሰዎች በየዩኒቨርሲቲው (መካነ ትምህርት) ከያዙት የወሳኝነት ሥልጣንና በፊደላቱ ዙሪያ ላሉ ነገሮች ሁሉ የሚመለከታቸው ወይም ተጠያቂዎች እነሱ እንደሆኑ ተደርጎ ከመታመኑ የተነሣ ያለ ዕውቀት ሳይገባቸው ትክክል መስሏቸው የሚወስኑት የተሳሳተ ውሳኔ ሥራ ላይ ሊውል የሚችልበት አጋጣሚና ሥጋት ወይም አደጋ በግልጽ እየታየ በመሆኑ ዝምታውንና ንቀቱን ወደ ጎን በመተው በቂና አጥጋቢ ምላሽ ሊሰጣቸው እንደሚገባ በማመን ከእናት ቤተ ክርስቲያን ያገኘሁትንና የማውቀውን ያህል ተገቢውን ምላሽ ሰጥቻለሁ፡፡ በቀጥታ ወደ ጥያቄዎቹ ልሒድና ጥያቄዎቻቸው በራሳቸው አገላለጽ የሚከተሉትን ይመስላሉ፡፡

    1. የፊደላቱ ብዛት ከሚገባው በላይ ተንዛዝቶና ገዝፎ እንዲታይ በመደረጉ በመማር ማስተማር ተግባር ላይ አላስፈላጊ ችግር ማለትም መሰላቸትን፣ መታከትን፣ መወሳሰብን፣ አስከትሏል፡፡ 2. ሞክሼ ፊደላት መኖራቸው በሥነ ጽሑፎቻችን ላይ የተዘበራረቀ የፊደላት አጠቃቀም እንዲከሰት አድርጓል፡፡ 3. የአናባቢ ወይም የድምፅ ሰጪ ምልክቶች ወጥ አለመሆን ወይም የተዘበራረቁ መሆናቸው እነእርሱን በቀላሉ ለማጥናት እንዳይቻል አድርጓል የሚሏቸው ጥያቄዎች ናቸው፡፡

    ነገር ግን ምሁራኑ ያልተረዱት ነገር ቢኖር አባቶቻችን ያለበቂና አጥጋቢ ምክንያት ያደረጉት አንድም ነገር እንደሌለ ያለማወቃቸውን ነው፡፡ አሁን ጥያቄዎቻቸውን በተናጠል ከበቂ መልሶቻቸው ጋር እንይ፡-

    ወደ መጀመርያው ጥያቄያቸው ወይም ቅሬታቸው ስናልፍ ማለትም የፊደላቱ ብዛት ከሚገባው በላይ ተንዛዝቶና ገዝፎ እንዲታይ በመደረጉ በመማር ማስተማር ተግባር ላይ አላስፈላጊ ችግር ማለትም መሰላቸት መታከት መወሳሰብ አስከትሏል ላሉት ችግር መፍትሔ አድርገው ያቀረቡት ነጥብ ሞክሼ ፊደላትን፣ ፍንድቅ ፊደላትን፣ የግእዝ ዲቃላ ፊደላትን በአጠቃላይ ከ91 በላይ ፊደላትን ማስወገድ ሲሆን አንዳንዶቹ ሻል ያሉቱ ደግሞ ፍንድቅ ፊደላትንና የግእዝ ዲቃላ ፊደላትን በምልክት መተካት ይላሉ፡፡ ይህን ጥያቄ ያነሡ ሰዎች ያልተረዷቸው ነገሮች ቢኖሩ፡-

    ሀ/ ቋንቋችን አቡጊዳዊ (syllabary) ማለትም አናባቢንና ተነባቢን በአንድ ፊደል የወከለና ፎነቲክ ማለትም በቋንቋው ውስጥ ላሉ ድምፆች ሁሉ ለእያንዳንዳቸው የየራሳቸውን ፊደል የሰጠ ወይም የቀረጸ ቋንቋ መሆኑን፡፡ በመሆኑም የፊደላቱ መበርከት ጨርሶ በጥያቄ መልክ ሊነሣ ባልተገባ ነበር፡፡ ምክንያቱም ይህ መሆኑ በዓለም ውስጥ ካሉ ቋንቋዎች እንዲደነቅ ያደረገውና ከማንኛውም ቋንቋ በተሻለ መልኩ ለብዙ ድምፆች ፊደል የቀረጸ በመባል በባዕዳን ምሁራን ሳይቀር ተደናቂ ያደረገው የቋንቋችን ባሕርይ መሆኑ ነው፡፡

    ለ/ አሁንም ያልተረዱት ነገር ቢኖር ፊደላቱ በዝተዋል በሚል ከ24 በላይ ፍንጽቅ ፊደላትንና 20 የግእዝ ዲቃላ ፊደላትን ይወገዱ ሲሉ የሚያስወግዷቸው ፊደላቱን ብቻ ሳይሆን በፊደላቱ የተወከሉትን በንግግሮቻችን ውስጥ ያሉ ድምፆችን ጭምር ይወገዱ ማለታቸው እንደሆነ ነው፡፡ ይህ ቢሆን ደግሞ የቋንቋውን ባሕርይና ምድቡንም ማለትም ከየትኛው የቋንቋ ዘር ውስጥ መሆኑን የሚገልጹትን ድምፆች እንዲያጣ ሊያደርገው መሆኑን፣ ቋንቋው ማለት የሚፈልገውን በቀላልና ግልጽ በሆነ መንገድ ማለት እንዳይችል ወይም እንዳይገልጽ ሊሆን መሆኑን፣ በጽሕፈት ላይም ከእነዚያ ከተወገዱት ፍንጽቅ ፊደላትና የግእዝ ዲቃላ ፊደላት አንዷ የምትገልጸውን ድምፅ በመወገዳቸው ምክንያት ይወክሉት የነበረውን ድምፅ ለመግለጽ ከዚህ በኋላ እንደ አልፋቤቲካዊ ወይም ተናጠላዊ ቋንቋዎች በሁለት ፊደላት መግለጽ ግዴታ በመሆኑ በአንድ ገጽ የሚያልቅ የነበረው ጽሑፍ ከአንድ ገጽ በላይ እንዲገልጽ ሊያስገድደን እንደሆነ ነው፡፡ ይህም በደራሲው በሐዲስ ዓለማየሁ መጽሐፍ በፍቅር እስከ መቃብር ታይቷል፡፡ እራሳቸው ሐዲስ ዓለማየሁም ቢሆኑ የዚህ ዓላማ አራማጅ ሆነውም ጨርሶ ችግር አያመጣም አላሉም፡፡ የሚያስከትለው የንባብ ችግር ወይም የምሥጢር መፋለስና መሰወር ችግር ይህን ያህል አይደለም አሉ እንጂ፡፡ ነገር ግን ትንሽም ቢሆን በትክክሉ ማስቀመጥ ሲቻል አንዲትስ ብትሆን ለምን አግባብ ያልሆነ እንከን እናስቀምጥ?፡፡ አባቶቻችን ያንን ያህል እርቀው በንግግር ላሉ ድምፆች ሁሉ ፊደል በመቅረጽ ያለችግር ማለት የተፈለገን ነገር በትክክል እንዲባል እስከማድረግ ድረስ ርቀው በመሔድ ያደራጇቸውን ፊደላት በመቀነስ ቀደም ሲል ያየነውንና ቀጥሎ የምናያቸውን ችግሮች እንዲከሰቱ ማድረግ ማንም ሊረዳው እንደሚችለው የቋንቋውን ዕድገትና ብቃት ወደ ኋላ መመለስ ወይም ማንሸራተት እንጂ ዕድገት ወይም ችግር መቅረፍ ሊሆን አይችልም፡፡

    አጥንቶ ለመያዝ ከአንድ ሰሞን በላይ የማይጠይቁትን ፊደላት ሲፈለጉ ብቻ ካልሆነ በስተቀር በፊደል ገበታቸው ቦታቸውን ይዘው አርፈው የተቀመጡትን ፊደላት አቀለልን በማለት ሲያስወግዷቸው ከዚያ በኋላ እነሱ ችግር ነው ከሚሉት በላይ መጽሐፍ ለመጻፍ ተጨማሪ ገጾችን መጠየቃቸው ይህም ደግሞ አንዳች ነገር ለመጻፍ በተፈለገ ጊዜ ሁሉ የግድ መሆኑ ከግለሰብ አልፎ በሀገር ጥሪት ወይም ኢኮኖሚ ላይ የሚያስከትለው አላስፈላጊ ወጪ ወይም ኪሣራ ጨርሶ አልታያቸውም፡፡ የዚህ ዓላማ አራማጅ የነበሩት ሐዲስ ዓለማየሁ መጽሐፋቸውን እንደዚህ አድርገው ይጻፉት እንጂ በንግግራቸው ግን ጨርሶ ሊተገብሩት አልቻሉም ነበር፡፡ ሊተገብሩትም አይችሉም፤ ምክንያቱም ቋንቋችን ፎነቲክ ነውና ማለትም ለእያንዳንዱ ድምፅ የየራሱን ፊደል የቀረጸና እንደ ፎነቲክነቱም ለእያንዳንዱ ድምፅ ፊደል የመቅረጽ ግዴታ ስላለበት፡፡ ቋንቋችን ፎነቲክ የሆንው በምርጫ ወይም ተፈልጎ አይደለም፤ ነገር ግን ተፈጥሯዊ ባሕርይው ስለሆነ እንጂ፡፡ ቋንቋችን በተፈጥሮው አቡጊዳዊ ወይም ሲለበሪ መሆኑ ነው ፊደሎቻችን አቡጊዳዊ ወይም ሲለበሪ ማለትም አናባቢና ተነባቢን በአንድ ፊደል የሚወክሉ እንዲሆኑ የተገደዱት፡፡ ፊደሎቻችን ሳይፈጠሩ በፊትም የቋንቋችን ድምፆች በተፈጥሯቸው ስንናገራቸው አናባቢና ተነባቢ በአንድ ላይ ተቀላቅለው ወይም ተደምረው ነው የሚወጡት፡፡ ለምሳሌ በድምፅ ውስጥ እራሱ ‹‹ብ›› እና ‹‹ኧ›› ድምፆች ተቀላቅለው ነው የሚወጡት፣ ቡ ስንል ደግሞ ‹‹ብ›› እና ‹‹ኡ፣ ቢ ስንል ደግሞ ‹‹ብ›› እና ‹‹ኢ›› በዚሁ መልኩ ሁሉንም ሆሔዎች ስንጠራ በውስጣቸው የአናባቢ ድምፆች አብረው ይኖራሉ፡፡ ይሄም በመሆኑ ነው ፊደል ሲቀረጽላቸውም አናባቢንና ተነባቢን በአንድነት የሚገልጹ ሆነው የተገኙት፡፡ ይሔ እንግዲህ ምንም ልናደርገው የማንችለው ተፈጥሯዊ ባሕርይው ነው፡፡

    ይህንን ከላይ የገለጽኩትን የቋንቋችንን ተፈጥሯዊ ባሕርይ የሚያውቅና የተረዳ ሰው በምንም ተአምር ቋንቋችን ለእያንዳንዱ ድምፅ ፊደል መቅረጹን ሊቃወም ወይም ላይቀበል አይችልም፡፡ ቀደም ሲል እንደገለጽኩት ቋንቋችን ለብዙ ድምፆች ለየራሳቸው ፊደል በመቅረጹ የሚያክለው ወይም የሚስተካከለው ቋንቋ ባለመኖሩ እጅግ ተደናቂ አድርጎታል፡፡ በመሆኑም ምሁራኑ ይህንን ጥያቄ ሲያነሡ እኔ የሚገባኝ ምንድ ነው? ሰዎቹ ምን ያህል የገዛ ቋንቋቸውን ባሕሪ በጥልቀት ያለመረዳታቸውንና ባልተረዱት ነገር ላይ ለውሳኔ መቸኮላቸውን ነው፡፡ በጣም የሚገርመው ደግሞ እነዚህ ሰዎች በቋንቋ ጥናት የዶክትሬትና የፕሮፌሰርነት ማዕርግ ከዚያም በላይ ያላቸው መሆናቸው ነው፡፡

    ሐ/ የቋንቋው የድምፅ ሥርዓት የሚበላሽ መሆኑን ማለትም አዳዲስና ከአማርኛ ቋንቋ የልሳን ድምፆች ውጭ የሆኑ ወይም ያልነበሩ የተንሻፈፈና የተወላገደ የአፍ አከፋፈት፣ የምላስ መተሣሠር የሚያስከትሉ አዳዲስ ድምፆች የሚከሠቱ መሆናቸውን፡፡ ለምሳሌ ባሏ ለማለት ባልዋ፣ ሲሟሟ ለማለት ሲሙዋሙዋ፣ ሲሯሯጡ ለማለት ሲሩዋሩዋጡ፣ እሷ ለማለት እሱዋ፣ ሿሚ ለማለት ሹዋሚ፣ ቋንቋ ለማለት ቁዋንቁዋ፣ ቧልት ለማለት ቡዋልት፣ ፊቷ ለማለት ፊቱዋ፣ ወንድሞቿ ለማለት ወንድሞቹዋ፣ ኋላ ለማለት ሁዋላ፣ ኗሪ ለማለት ኑዋሪ፣ እንኳን ለማለት እንኩዋን፣ ዟሪ ለማለት ዙዋሪ፣ አንዷ ለማለት አንዱዋ፣ እጇ ለማለት እጁዋ፣ ጓደኛ ለማለት ጉዋደኛ፣ ጧሪ ለማለት ጡዋሪ፣ ጯሂ ለማለት ጩዋሂ፣ ፏፏቴ ለማለት ፉዋፉዋቴ ወዘተ እየተባሉ ሲጻፉ ሲነገሩ ሲነበቡ ማንም እንደሚገነዘበው ለአንደበት ካለመመቸታቸውም ባሻገር ለጆሮ የሚሰጡት የድምፅ ቃና ጥሩ ባለመሆኑ የቋንቋችንን የጥራት ደረጃ የሚያወርድ የሚያጎል እንጂ እሴት የሚጨምር አለመሆኑን፡፡

    መ/ ሞክሼ ፊደላት ቢወገዱ የሚከሰቱትን የምሥጢርና የትርጉም መፋለስን፡፡ ሞክሼ ፊደላትንም አባቶቻችን ያለጥቅምና ያለበቂ ምክንያት እንዳልፈጠሯቸው መረዳት አልተቻላቸውም፡፡ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሞክሼ ፊደላት አጠቃቀም የራሳቸው የሆነ ዶግማዊ አይዶሎጂያዊ ወይም ርእዮተ ዓለማዊ እና መለያዊ ምክንያቶች ያላቸው ናቸው፡፡ እነዚህን ሦስት ምክንያቶች በምሳሌ እንይ፡- በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ አምስት አዕማደ ምሥጢራት አሉ፡፡ ከእነዚህ ሦስቱ በፊደላት አጠቃቀም የታሠሩ ናቸው፡፡ እነዚህም ምሥጢረ ሥላሴ፣ ምሥጢረ ሥጋዌ እና ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታን ናቸው፡፡ ወደ ምሥጢረ ሥላሴ ስንሔድ ሦስቱ ቁጥር በፊደል ሲጻፍ በንጉሡ ሠ ወይም በሠራዊቱ ሠ ሳብዑ ነው፡፡ ሥላሴ የሚለው ቃልም ሲጻፍ በንጉሡ ሥ ነው፡፡

    ሥላሴና ሦስት በአንድ የሠ ቤት መጻፋቸው ሥላሴ አንድም ሦስትም ናቸው የሚለውን ዶግማዊ አስተምህሮ እንዲገልጽና እንዲይዝ በማሰብ ነው፡፡ ከዚህ ወጥቶ ግን በእሳቱ ሳ ቢጻፍ የሚገልጹት ቃል ወይም ትርጉም ሌላ ይሆናል፡፡ ምሥጢረ ሥጋዌ ሲጻፍም በንጉሡ ወይም በሠራዊቱ ሠ ሳድሱ ነው፡፡ ሥጋ ሲጻፍም በዚያው ሥ ነው፡፡ የዚህ ምክንያቱ ሥጋ በተጻፈበት ሥጋዌ መጻፉ ‹‹መለኮት ሰው ሆነ ሥጋ ለበሰ›› የሚለውን ዶግማዊ ምሥጢር እንዲይዝ ታስቦ ነው፡፡ ትንሣኤ ሲጻፍ የሚጻፈው በንጉሡ ሥ ራብዑ ነው፡፡ ትንሣኤ ማለት መነሣት ማለት ነው፡፡ በዚሁ ‹‹ሣ›› መጻፉ ቀርቶ በእሳቱ ‹‹ሳ›› ቢጻፍ መነሣት የሚለው ትርጉም ይቀርና አከላከል ወይም መከልከል የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ ይህም በመሆኑ ምሥጢር ይፋለሳል፣ መባል የተፈለገው ሳይባል መባል ያልተፈለገው ይባላል ማለት ነው፡፡ ሌሎችም እንደዚሁ ፊደላቱ ቢለዋወጡ ችግር የሚያመጡ ኅቡአት የእግዚአብሔር ስሞች ብዙ አሉ፡፡ ከዶግማዊ ምክንያቶች እነዚህን ካነሣን ይበቃል፡፡ ወደ አይዶሎጂያዊ ወይም ርእዮተ ዓለማዊ ምክንያቶች ስንሔድ ደግሞ ክቧ ዐ ዐይኗ ዐ በመባል ትታወቃለች፤ ዐይን ሲጻፍም የሚጻፈው በዚህችው ዐ ነው፡፡ ዐይኗ ዐ የተባለችበት ምክንያትም የዐይን ቅርጽ በመያዟ ወይም ዐይን በመምሰሏ ምክንያት ነው፡፡

    ወደመለያዊ ምክንያት ስንሔድ ደግሞ በአል የሚለው ቃል በአልፋው አ ሲጻፍ አይሁድ ያመልኩት የነበረን ጣዖት ስም ያመለክታል፡፡ በዓይኑ ዐ ራብዑ ሲጻፍ ደግሞ ልዩ ቀን የተከበረ ቀን የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ ዓመት የሚለው ቃል በዐይኑ ዐ ራብዑ ሲጻፍ 12 ወራት ከ5 ወይም ከ6 ቀናት ማለት ሲሆን፣ ዓመት የሚለው ቃል በአልፋው አ ሲጻፍ ደግሞ አገልጋይ የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ ‹‹አኅያ›› ማለት የእግዚአብሔር ኅቡእ ስሙ ነው፡፡ ሲነበብም ላልቶ ነው የሚነበበው ‹‹አህያ›› ደግሞ ከእንስሳት አንዱ የበቅሎ አባት ወይም የፈረስ አጎት ማለት ነው፡፡

    ሠዓሊ የሚለው ቃል በንጉሡ ሠ እና በዓይኑ ዐ ራብዑ ሲጻፍ ሥዕል የመሣል ሙያ ያለው ማለት ሲሆን፣ ሰአሊ የሚለው ቃል በእሳቱ ሰ እና በአልፋው አ ሲጻፍ ደግሞ ለማኝ፣ ተማጻኝ የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ አራት በአልፋው አ ሲጻፍ ከሦስት ቀጥሎ የሚገኝን ቁጥር ሲያመለክት በዐይኑ ዐ ሲጻፍ ደግሞ መኝታ የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ ሠረቀ የሚለው ቃል በንጉሡ ሠ ሲጻፍ ወጣ፣ ታየ፣ ተገለጠ፣ ብቅ አለ፣ በራ የሚል ትርጉም ሲኖረው በእሳቱ ሰ ሲጻፍ ደግሞ ለበየ፣ ወሰደ፣ አጠፋ፣ ደበቀ፣ የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ ምሁር የሚለው ቃል በሀሌታው ሀ ሲጻፍ የተማረ ያወቀ የመጠቀ የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ በሐመሩ ሐ ካዕቡ ሲጻፍ ደግሞ ምሕረት ያገኘ የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ እነዚህን የመሳሰሉ ብዙ ቃላት አሉ፡፡ እንግዲህ በግልጽ እንደሚታየው አባቶቻችን ይህን ያደረጉበት ወይም ሞክሼ ፊደላትን የፈጠሩበት ምክንያት የቃላት መመሳሰል ሲያጋጥም በፈደላቱ በመለያየት የየራሳቸውን ትርጉም እንዲይዙና አሻሚ እንዳይሆኑ ለማድረግ ነው፡፡ የሞክሼ ፊደላት አገልግሎት ይሄ ነው እንጂ ቀድሞ የተለየ ድምፅ ኖሯቸው ያድምፃቸው አሁን ጠፍቶ ወይም ተረስቶ አይደለም፣ ይህ አስተሳሰብ የተለየ ድምፅ ከነበራቸው አሁን ላይ ያ ድምፃቸው ጠፍቷልና ወይም ተረስቷልና ፊደላቱ ጥቅም የላቸውም ማለት ነው፤ ስለዚህም ይወገዱ ለማለት የተፈጠረ ሰበብ ነው፡፡ እውነቱና የፊደላቱ አገልግሎት ግን ከላይ በምሣሌዎች እንዳየናቸው ነው፡፡

    ምሁራኑ ግን ፊደላቱ ያላቸውን አገልግሎትና ቢጐሉ የሚያስከትሉትን ችግር ባለማጤን ወይም ባለማወቅ እንደ ትርፍና አላስፈላጊ ቆጥረዋቸዋል፡፡ እነኚህ ምሁራን በእንደነዚህ ዓይነት ማብራሪያዎች ወገባቸው ሲያዝ አሁን አሁን ደግሞ ምን ማለት ጀምረዋል? እሺ ለግእዝስ ይሁን ሞክሼ ፊደላት ለአማርኛ ግን አይጠቅሙምና ከአማርኛ ይወገዱ ማለት ጀምረዋል፡፡ አሁንም ቢሆን ግን አንድ ያልተረዱት ጉዳይ አለ፡፡ እሱም አማርኛ ቋንቋ በራሱ የቆመ ቋንቋ አለመሆኑን ወይም ያለግዕዝ ድጋፍ ቋንቋ ሆኖ ማገልገል የማይችል መሆኑን፣ ከግሶቹ እና ቃላቱ የሚበዙቱ ግእዝ መሆናቸውን አለማወቅ፣ ከግእዝ ፈጽሞ መነጠል የማይችል ወይም እራሱን የቻለ ቋንቋ አለመሆኑን ያለመረዳታቸውና በዚህ ምክንያትም የሞክሼ ፊደላቱን አገልግሎት የግዱን የሚጋራ መሆኑን ካለማወቅ የተነሣ ይህንን ሲሉ ይደመጣሉ፡፡ በአጠቃላይ ችግር ነው ብለው የሚገልጹትና መፍትሔ ነው ብለው የሚያቀርቡት አራምባና ቆቦ እንደሚባለው የማይገናኙ ብቻ ሳይሆኑ በተቃራኒው አቅጣጫ ሲነጉዱ ይታያል፡፡

    ከእነዚህኞቹ የተሻሉ ናቸው የተባሉት ፍንጽቅ ፊደላትንና የግእዝ ዲቃላ ፊደላትን ከማስወገድ ይልቅ በምልክት መተካት የሚሉቱ ለእንዲህ አይነት ውሳኔ የዳረጋቸው ምክንያትና ድርጊታቸው ወይም ውሳኔያቸው ፈጽሞ የሚጣጣም አይደለም፤ እነሱ እንዲህ እንዲሆን የፈለጉበትን ምክንያት ሲገልጹ ፊደሎቹ በጣም ከመብዛታቸው የተነሣ ለጀማሪ ፊደል ቆጣሪ የተወሳሰበ አድርጎታል ብለው ሲያበቁ ለመፍትሔአቸውም ሲሉ የፊደላቱን ቁጥር መቀነስ ላይ ብቻ ሲያተኩሩ መወሳሰብን ለማስወገድ ያሉትን የመፍትሔ መንሥኤያቸውን እረስተውት ከአርባ በላይ ፊደላትን በወረቀት ላይ ግዘፈ አካል ነስተው የሚታዩና የሚታወቁ የነበሩትን ፊደላትን በአንዲት ምልክት ተክተው የማይታዩ አደረጓቸው፣ ይሄም መሆኑ ጭራሽ እንኳን ለጀማሪ ፊደል ቆጣሪ ይቅርና ፊደል ለለየውም እንኳን ከአርባ በላይ የተለያዩ ድምፆችና የተለያዩ የድምፅ ቅላጼ ወይም ፎኒም ያላቸውን ፊደላት አንድ ምልክትን ከሀ ለ ሐ መ ው ካሉት አምሳያ ፊደሎቻቸው ጋር በማቀናጀትና በመጠቀም ከአርባ በላይ የፍንጽቅ ፊደላትንና የግእዝ ዲቃላ ፊደላትን እንዲፈጥሩ ማድረግ በጣም የተወሳሰበና ከባድ አደናገሪም እንዲሆን ማድረጋቸው ጨርሶ ሳይታወቃቸው ቀርቶል፡፡ ልብ በሉ ይህንን ያደረጉት ግን መወሳሰብን ለማስወገድ በሚል ነው፡፡

    ውጤቱ ግን የተገላቢጦሽ ሆኖ ቁጭ አለ፡፡ ችግር ነው ብለው የሚያወሩትና መፍትሔ ነው ብለው የሚያቀርቡት ሐሳብ ጨርሶ ባለመጣጣሙ እነዚህ ሰዎች ደኅና የነበረውን መፍትሔ ነው እያሉ ጭራሽ የተወሳሰበ ችግር የሚፈጥሩበት እንዲህ የሚያደርጋቸው ፊደላቱን የሚያስጠላቸው ዐይነ ጥላ ይሆን ያሰኛል፡፡ ወደ ሁለተኛው የፊደል ገበታችን አለበት ወደ አሉት ችግር ስናልፍ፡-

    በሥነ ጽሑፎቻችን ላይ የተዘበራረቀ የፊደላት አጠቃ

Leave a Reply

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

Archives

Copyright and Disclaimer

Copyright © 2010 - 2015 Kefale Alemu

Copyright © [2010]. KAlemu, All Rights Reserved.