ስለ ሰምና ወርቅ (ቅኔ) አመጣጥ አስደናቂ ታሪክና ትምህርት

የሰዉ ልጅ  ከምድራዊ ፍጥረታት እና ከሁሉም  እንሰሳት የሚለየዉ  ከአራቱ  ባህሪያት መፈጠሩና  በልሳነ -ሰብ (በአንደበታዊ  ንግግር ) በቓንቓ መግባባት መቻሉ ነዉ፡፡

ንግግርን ወይንም በቓንቓ መግባባትትን  የጀመሩት ከፍጥረታት ሁሉ  የመጀመሪያ  ፍጥረት የሆኑት መላእክቶች  ሲሆኑ የተግባቡትም በግዕዝ ቓንቓ ነበረ ይህ የመጀመሪያ ቓንቓ ግዕዝ ታዲያ  ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ልዴት በፊት የግብጽ ፈርኦኖች ጡብ ሲገነቡና ሰማይ እንደርሳለን አብ ወልድ መንፈስቅዱስን በጦር እንወጋለን እያሉ እስራኤልን ሲየስቀጠቅጡ ግፍ ሲያበዙባቸዉ ቓንቓዉ ወደ ሰባሁለት ተከፈለ ፡፡ ኢትዮጵያዉያን ግን ይህንቓንቓ በእግዚአብሄርና በመላእክት እርዳታ ከአማርኛ ጋር እስካሁን ጠብቀው ይጠቀሙበታል። ይኽ የመላእክት ቀደምት ቓንቓ ምስጢር አዘል መልእክትን በአጭር ቃላት ማስተላለፍ የሚችል ሰምና ወርቅ ንግግርን በግእዝም በአማረኛም ይዞ የሚገኝ ሲሆን  አሁን በዚህ ጽሁፍ የምናቀርበዉ ለተማሪዎች መምህራንና እንዲሁም ለቓንቓዉ እንግዳ የሆኑ ሰዎች ሰምና ወርቅን ጠንቅቀዉ ማወቅ ለሚፈልጉ ሁሉ በቀላሉ እንዲገባቸዉና የአማረኛ ቅኔን የአፈታት ስልቶች በግልጽእንዲረዱት ተደርጎ የተዘጋጀ ነው።

የአማረኛ ቅኔ (ሰምናወርቅ) አጭር የአማረኛ ንግግር ክፍል ሲሆን በዉስን ቃላት ፣ ሀረጋት፣ ስንኝና ስድ ጽሑፍ ወዘተ ከባድና ስዉር መልዕክት የምናስተላልፍበት ልዩና ምርጥ መሳሪያ ነው ፡፡

ሠምና ወርቅ ስንል ሰም ማለት ሰምአ ሰማ (ሰምነከረ ፣ሰራ) ካለው የግዕዝ ቃል የመጣ ሲሆን ጥሬ ትርጉሙ በአማረኛ  ሰም ማለት ከማር ጣጭ (ጭማቂ) ተነጥሮ የሚዘጋጅ ለጻፍና ጡዋፍን ለመስራት የምንጠቀምበት ጥሩ ሽታ ያለው ቁስ ማለት ሲሆን ወርቅ ማለት ደግሞ መአድን በቁፋሮ ከመሬት ውስጥ የሚገኝ ልፋት፣ጥረትና ድካን የሚጠይቅ አንጸባራቂ አጥበርባሪ የሚያምርና ውብ ማራኪ መልክ ያለው ውድ የሆነ ቁስ መሆኑ ለማንም ግልጽ ቢሆንም በአማረኛ አገባቡ ግን ልዩ ነው ፡፡ ወርቅ ወቅነቱ የሚታወቀው በእሳት ሲፈተን እነደመሆኑ መጠን በአማረኛ ንግግርም ወርቅን ለማወቅና ለመገንዘብ ጊዜና ጥረትን; አቅምን ፣ብልህነትን ፣ማሰብን ፣ክህሎትን እና ፍላጎትን ወዘተ የሚጠይቅ ከታወቀ በኃላ ግን ልዩ አቅምን የሚፈጥርና ሰውን የዕውቀት ማህደር የማድረግ የሚችል ነው

በመሆኑም የሃገሪቱን ወግ፣ ባህል፣ ልማድ፣ ጀግንነት፣ ሐዘን፣ ደስታ፣ ታሪክና የት መጣሽነት ወዘተርፈ በግጥም (በስንኝ)፣ በስድ ንባብና በመሳሰሉትሲያወሳ እና ሲዘክር ይኖራል ፡፡

ይኽ የአማረኛ ት/ት ክፍል ለምርምር ፣ለት/ት እና መድኃኒት ቅመማ ፣ለፈጠራና ሰነ-ጽሑፍ እንድሁም ለዜማና ድርሰት ሙያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው ቓነቓ ነው፡፡

ሠምና ወርቅ በሁለት ይከፈላል

  1. የግዕዝ ሠምና ወርቅ
  1. የአማረኛ ሰምና ወርቅ ናቸው ፡፡

ሰም በአማረኛ ጥሬ ትርጉሙ በቀጥታ የምናገኘው የቃሉ እማሬዊ (አውዳዊ) ፍች ማለት ሲሆን ወርቅ ማለት ደግሞ ህበዕ(ስውር)፣ ድብቅ ሆኖ ያለ በፍለጋና በማሰብ የሚደረስበት የቃሉ ሁለተኛ ትርጉም (ልዩ መልእክት) ወይም የቃሉ ፍካሬያዊ ፍች ማለት ነው ፡፡

ይኽም በሰም ተሸፍኖ በኅብረ ቃል  አጊጦ ና ተወቦ ይገኛል ፡፡

የአማረኛ ሰምና ወርቅን ለማወቅ ሶስት ነገሮችን ልብ ማለት ይጠበቅብናል ፡፡

ሀ. ሰም

ለ. ወርቅ

ሐ. ሕብረቃል

እንደዚሁም የአፈታት ስልቶችን በዚህረገድ በርካታ ምሁራኖች ስለ ቅኔ ሰምና ወርቅ በርካታ ነገር ይጻፉ እንጅ የአማረኛ ቅኔዎችን በመፍታት ዙሪያ ምንም ቢሆን ስራ ተሰርተል ማለት አንችልም አሁን ግን የተማሪዎችን ፣መ/ን እና ተመራማሪዎችን ችግር የሆነውን የአማረኛ ቅኔ አፈታት ስልት በመገንዘብና ለሰራው ምቹ ሁኔታን ከመፈጠር አንጻር ይህ ጽሁፍ ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል፡፡

ቀደም  ብለው የተጻፉ  መጻሕፍትን እና መረጃዎችን ስናይ በብዛት ስለቅኔው እንጅ ስለአፈታቱ  ያስቀመጡት በቂ መረጃ አለ ለማለት አያስደፍርም  ፡፡

ስለሆነም ከገጠሙን ችግሮች እና ከምናያቸው የመጨረሻም ባይሆን በዚህ ትውልድ ያለውን የቅኔ (ሰምና ወርቅ) የመለየትና የአፈታት ችግር ይኽ መጽሐፍ በመጠኑም ቢሆን በር ይከፍታል ብየ አምናለሁ  ፡፡

አራት የአፈታት ዘዴወች ፡፡

ታሪክን በማወቅ::  ከመጽሐ ቅዱስ፣ ከቁራን ከታሪክ መጻሕፍትና ከአባቶች  ወዘተ

መቅዴላ አፋፉ ላይጩኸት በረከተ ፣

የሴቱን አናውቅም  ወንድ አንድ ሰው ሞተ ፡፡

የቅኔው አይነት የኀዘን ቅኔ  ሲሆን አፈታቱ ታሪክን በማወቅ ይሆናል ፡፡

ሕብረ ቃሉ- ወንድ አንድ ሰው  የሚለው ነው ፡፡

ታሪኩ መቅዴላ ታላቅ ስራ የሰራው  አጼ -ቴዎድሮስ ነው !!

ሠሙ፡-መቅዴላ አፋፍ ከፍተኛ ለቅሶና ጩኸ  አለ የሞተው ወንድ በቁጥር አንድ ሲሆን ምንያህል ሴት እነዴሞተ  አልታወቀም የሚል ነው ፡፡

ወርቁ፡- ጀግናው አጼ-ቴዎድሮስ ሞተ የሚል ነው ፡፡

ምሳሌ 

ሊበላ ብሎ አንበጣ ፣

ራዛው በላይ መጣ ፡፡

ሕብረ ቃሉ- ራዛው በላይ መጣ

ሠሙ፡- አንበጣው አዝመራውን ሊበላ ሲል ራዛ የተባለው አሞራ በሰመይ መጣበት የሚል ነው ፡፡

ወርቁ፡- ጣሊያን ኢትዮጵያን ለቅኝ ግዛት እወራለሁ ሲል ጀግናው በላይ ዘለቀ ለቃቅሞ ጨረሰው ማለት ነው ፡፡

የቅኔው አፈታት ስልት ታሪክን በማወቅና ነገሮችን በማመሳሰል የመፍታት ስልት ነው ፡፡

ራዛ ማለት ትልቅና ፈጣን አሞራ ነው

ለዚህም ነው ጀግናውና ወደርየለሹ በለይ ዘለቀ በፍጥነቱና ቅልጥፍናው በራዛ የተመሠለው ፡፡

ምሣሌ 

አጼ-ዮሃንስ ይዋሻሉ

መጠጥ አልጠጣም እያሉ ፣

ሲጠጡ አይተናል በእርግጥ ፣

ራስ እሚያዞር መጠጥ ፡፡

የአፈታት ስልቱ ታሪክን በማወቅ ነው ፡፡

ሕብረ -ቃል -ራስ እሚያዞር መጠጥ

ሠሙ -ንጉሱ አጼ-ዮሃንስ መጠጥ አልጠጣም ብለው ይዋሻሉ(ውሸት ያወራሉ)ነገር ግን ተደብቀው ሲጠጡ ታይተዋል ማለት ነው ፡፡

ወርቁ፡-1) ንጉሡ ዮሃንስ ከሱዳኖች ሲዋጉ አንገታቸዉ ተቆረጦ በሱዳኖች ተወሰደ ማለትም ሱዳን ድረስ ጭንቅላታቸው ተነከራተተ (ዞረ) ማለት ነው፡፡

ቃላትን አጥብቆና አላልቶ በማንበብ የመፍታት ዘዴ

ቻይና ማበር ገባች ያባቱዋም ልነበር ፣

እነሱን መጋበዝ ቡን አድርጎ ነበር ፡፡

ሕብረ -ቃል -ቡን አድርጎ ነበር

አፈታቱ ቃሉን አጥብቀንና አላልተን ስናነበው በሚያመጣው የትርጉም ለውጥ ነው ፡፡

ሠሙ -ቻይናወችን መጋበዝ ቡና አፍልቶ ነበር  ብሎ መቆጨቱን ይገልጻል ፡፡

ወርቁ- ቻይናዎች በተለያየ ምክንያት ወደ ሀገራችን ገቡ ቡን (አመድ) አድርገን ነበር ማጥፋት የሚል የቁጭት ስሜት ይገልጻል ፡፡

በተጨማሪም ቃላትን በመፈልቀቅ ፣ነገሮችን በመመሰልና ቦታና ጊዜን በማስታወስ የአማረኛ ሰምና ወርቅ ቅኔን መፈታት ይቻላል ፡፡

ይቀጥላል!!

Leave a Reply

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

Archives

Copyright and Disclaimer

Copyright © 2010 - 2015 Kefale Alemu

Copyright © [2010]. KAlemu, All Rights Reserved.